እርዳታ ለተፈናቃዮች
ማክሰኞ፣ ጥር 29 2010በሪያድ እና አካባቢው በሚኖሩ የኦሮሞ ቄሮዎች ወይንም ወጣቶች አስተባባሪነት ሪያድ ከተማ ውስጥ በተደረገው የድጋፍ ማሰባሰብ መርሐ ግብር ልባቸው የተነካ የባሌ ዞን ተወላጆች ወርቅ እና ጌጦቻቸውንም ሆነ የለበሱትን ጃኬት አውልቀው ለወገኖቻችን ይድረስልን ያሉ በርካታ ናቸው፡፡ በአካባቢው የተፈጠረውን ችግር በተመለከተ ወቅታዊ እና ተጨባጭ እውነታውን ለመረዳትም ወኪሎቻቸውን ልከው እንደነበር አዘጋጆቹ ይናገራሉ
ከሰባት መቶ ሺህ በላይ የኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ተፈናቅለውበታል በተባለው የኦሮሚያ እና የሶማሌ ክልል ግጭት ከባሌ ዞን ቆላማ አካባቢዎች ከአንድመቶ አስራ ሶስት ሺህ በላይ ኦሮሞዎች ተፈናቅለዋል ፡፡ ሪያድ ለሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች የደረሰው መረጃ እንደሚያሳየው ታዲያ እስካሁን ይህ ነው የሚባል ድጋፍ አላገኙም ፡፡ የአካባቢው ተወላጅ አቶ ሙስጠፋ ሁሴን እንደሚናገሩት ዛሬም በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ ናቸው፡፡
አቶ አወል አህመድም ከአስተባባሪዎቹ አንዱ ናቸው ፡፡ አሳቸው እንዳሉት ደግሞ የአካባቢው ቆላነት፣ ስፋት፣ ከመንገድም ሆነ ከመሰረተ ልማት መራቅ ችግራቸውን ውስብስብ አድርጎታል፡፡
መምህር አብዱል ፈታህ አብዲ በድጋፍ ማሰባሰብ መርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል ፡፡ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ውጭ ሀገር ያለው ወገን ሀገር ውስጥ ከተፈናቀሉት የተሸለ ነው በመሆኑም አለንላችሁ የማለት ሃላፊነት የማንኛውም ኢትዮጵያዊ መሆን ይኖርበታል ይላሉ፡፡
በድጋፍ ማሰባሰቢያው ላይ የተገኙት ወጣጦች ጎልማሶችም ሆኑ አዛውንቶች ከ አምስት መቶ እስከ አምስት ሺህ የሳዑዲ ሪያል ለግሰዋል ፡፡
አስተባባሪዎቹ እንዳሉት ከሁለት ኮንቴይነር በላይ የሚሆኑ የህጻናት የሴቶችም ሆነ የወንዶች አልባሳት እንዲሁም የምሽት ልብሶች በልግስና ተገኝተዋል ፡፡ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ የድጋፍ ደብዳቤ በመያዝ ለተረጂዎቹ በተቻለ ፍጥነት የማድረስ ተግባር በቀጣይነት እንደሚያከናውኑ አስታውቀዋል፡፡
ስለሺ ሽብሩ
ኂሩት መለሰ