1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በመስቀል አደባባዩ የቦምብ ፍንዳታ 4 ሰዎች ሞተዋል - የዓይን እማኝ

እሑድ፣ ሰኔ 17 2010

ትናንት በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ላይ በደረሰው የቦምብ ፍንዳታ አራት ሰዎች መሞታቸውን መመልከታቸውን አንድ የአይን እማኝ ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። የኢትዮጵያ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ምኒስትር ዴኤታው አቶ ከበደ ወርቁ ግን የሞቱት ሁለት ብቻ መሆናቸውን ገልጸዋል።

https://p.dw.com/p/30Bo1
Äthiopien, Opfer von Granatenangriffen bei der Pro PM Abiy Ahmed Rallye
ምስል DW/G.Tedla Hailegiorgis

መንግሥት የሞቱት 2 ብቻ መሆናቸውን ገልጿል

ትናንት ቅዳሜ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ. ም. በመስቀል አደባባይ በነበረው የድጋፍ ሰልፍ ላይ በደረሰው የቦምብ ፍንዳታ አራት ሰዎች መሞታቸውን አንድ የአይን እማኝ ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። ከሰላሌ ተጉዘው በሰላማዊ ሰልፉ ላይ መሳተፋቸውን የሚናገሩት አቶ አባይ ተስፋዬ የተባሉት እኚሁ የዓይን እማኝ በፍንዳታው ጉዳት ደርሶባቸዋል።አቶ አባይ "ዶክተር አብይ አውርቶ ሲጨርስ ፈንጂ ለቀቁብኝ። እኔ ጋር የነበሩት አራት ሰዎች ናቸው። አራቱ ሰዎች ወዲያውኑ ሞቱ። እኔ ተረፍኩ" ብለዋል። የኢትዮጵያ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ምኒስትር ደዔታው አቶ ከበደ ወርቁ ግን የሞቱ ሰዎች ቁጥር 2 ብቻ መሆኑን ተናግረዋል።

እንደ አቶ አባይ ሁሉ በዘውዲቱ ዘውዲቱ ሆስፒታል ተኝተው ህክምናቸውን እየተከታተሉ የሚገኙት አቶ ግርማ ተክሉ የተባሉ የሰልፉ ተሳታፊ "ሰላም ነው ብለን ደም እንደሚፈስ ሳናውቅ መጥተን" ጉዳት ደረሰብን ሲሉ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል። አቶ ግርማ በቦምብ ፍንጣሪ አፋቸው እና እግራቸው ላይ መቁሰላቸውን ገልጸዋል። "ዶክተር አብይ ንግግሩን ጨርሶ ተሰናብቶ ፊቴን ልክ ወደቤቴ እንዳዞርኩኝ አንድ እግሬን ሳላነሳ ድው አለ በቃ፤ ጭለማ ሆነብን" ሲሉ በጊዜው የነበረውን ሁኔታ አስረድተዋል። 

የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ ያጠናቀረውን ዝርዝር ዘገባ ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ። 

ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ

እሸቴ በቀለ