1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቆሻሻን ወደ ብሉኬት የሚቀይረው የቴክኖሎጅ ኩባንያ ተሸለመ

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 18 2015

ዓለም አቀፉ የጀማሪ ቴክኖሎጅ ኩባንያዎች ሽልማት ድርጅት በተለያዩ ዘርፎች አሸናፊዎችን በቅርቡ ይፋ አድርጓል።ከነዚህም መካከል መሰረቱን ኢትዮጵያ እና ኬንያ ያደረገው እና በአካባቢ ጥበቃ ላይ የሚሰራው፤ኪዩቢክ የተባለው ጀማሪ የቴክኖሎጂ ኩባንያ የ2023 ዓ/ም የዓመቱ ምርጥ የቴክኖሎጅ ኩባንያ በመባል በውድድሩ አሸናፊ ሆኗል።

https://p.dw.com/p/4QYHv
Dänemark l Kubik gewinnt Startup des Jahres bei den Global Startup Awards!
አቶ ቅዱስ አስፋው በዴንማርክ ኮፐንሀገን ሽልማቱን ሲቀበል ምስል Global Startup Awards

ኩዩቢክ፤ የዓመቱ ምርጥ የቴክኖሎጅ ኩባንያ

በየዓመቱ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የጀማሪ ቴክኖሎጅዎች ውድድር በዘንድሮው ዓመት በአካባቢ ጥበቃ ላይ የሚሰራ እና ኪዩቢክ የተባለ ጀማሪ የቴክኖሎጅ ኩባንያ የዓመቱ ምርጥ በመባል አሸናፊ ሆኗል።የዛሬው የሳይንስና ቴክኖሎጅ ዝግጅትም የአሸናፊውን የቴክኖሎጅ  ኩባንያ ተባባሪ መስራች እና ዋና ስራ አስኪያጅ በማነጋገር  ተቀናብሯል። 
ዓለም አቀፉ የጀማሪ ቴክኖሎጅ ኩባንያዎች  ሽልማት ድርጅት /The Global Startup Awards/በተለያዩ ሀገራት ለሚገኙ የወደፊቱን ዲጂታል ዘመን ለሚወስኑ እና በማህበረሰብ ህይወት ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድሩ ቴክኖሎጅዎችን በማወዳደር  በየዓመቱ እውቅና ይሰጣል።ከአራት አህጎሮች እና ከ120 ሀገራት ተወዳዳሪዎችን  የሚያሳትፈው ይህ ድርጅት በተለያዩ ዘርፎች አሸናፊዎችን በቅርቡ ይፋ አድርጓል። ከነዚህም መካከል መሰረቱን ኢትዮጵያ እና ኬንያ ያደረገው ኪዩቢክ የተባለ በአካባቢ ጥበቃ ላይ የሚሰራ ጀማሪ የቴክኖሎጂ ኩባንያ  የ2023 ዓ/ም የዓመቱ ምርጥ የቴክኖሎጅ ኩባንያ በመባል በውድድሩ አሸናፊ ሆኗል።

Dänemark l Kubik gewinnt Startup des Jahres bei den Global Startup Awards!
የ2023 ዓለም አቀፍ የጀማሪ ቴክኖሎጅ ሽልማት ምስል Global Startup Awards

የፕላስቲክ ቆሻሻን በዝቅተኛ ካርቦን፣ለረጅም ጊዜ ሊያገለግሉ ወደሚችሉ የግንባታ እቃዎች የሚቀይረው ይህ ኩባንያ፤ከስምንት የመጨረሻ እጩዎች መካከል አንዱ በመሆን ከምድቡ አሸናፊ ሆኖ በጎርጎሪያኑ መጋቢት 29 ቀን 2023 ዓ/ም  በዴንማርክ መዲና በኮፐንሃገን በተካሄደ ታላቅ ስነ ስርዓት ተሸልሟል። የኩባንያው ተባባሪ መስራች እና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቅዱስ አስፋው እንደሚሉት ኪዩቢክ፤ ውድድሩን ያሸነፈው የተለያዩ ደረጃዎችን በማለፍ ከ7 ሺህ ተወዳዳሪዎች መካከል ነው። 
«ከ7 ሺህ ድርጅቶች መካከል ነው ለማሸነፍ  የቻልነው።«ኮምፒቲሽኑ» የጀመረው በፈረንጆቹ አቆጣጠር 2021 ዓ/ም ነበር።ያኔ «ኖሚኔትድ» ሆነን የኢስት አፍሪካን «ቻፕተር» አሸንፈን ነበር።ከዚያ በኋላ ለአፍካ ውድድር ቀረብን ያንንም ሰኔ 2022 ዓ/ም አሸነፍን።ኬፕታውን ሄደን።ብዙ ድጋፍ አግንተን ነበር።» ካሉ በኋላ በመጨረሻ የአሁኑን ሽልማት ማግኜታቸውን አቶ ቅዱስ አብራርተዋል።ከሁለት ዓመት በፊት በጎርጎሪያኑ 2021 ዓ/ም በአቶ ቅዱስ አስፋው እና ፔንዳ ማሪ በተባሉ ባልደረባቸው የተቋቋመው ኪዩቢክ፤ ጥቅም ላይ የማይውሉ ፕላስቲኮችን ቢም፣ እና  ቡሉኬትን ወደ መሳሰሉ የግንባታ ቁሳቁሶች በመቀየር  በሚሊዮን ቶን የሚቆጠር የፕላስቲክ ቆሻሻን ከአካባቢ የማስወገድ ዓላማ አለው። 

Kenia Äthiopien Start-Up l Kubik Technology l CEO und Mitgründer Kidus Asfaw
አቶ ቅዱስ አስፋው የኪዩቢክ ተባባሪ መስራች እና ዋና ስራ አስኪያጅ ምስል privat

በዚህ ሁኔታ በተመጣጣኝ ዋጋ የቤት መስሪያ ቁሳቁሶችን በማቅረብ የመኖሪያ ቤት ችግርን ለማቃለል እና የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ ይሰራል።በሌላ በኩል በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ ሴቶችም የስራ ዕድልን ይፈጥራል። በእነዚህ  ስራዎቹ ወይም እንደ አቶ ቅዱስ አባባል የድርጅቱ ልብ  በሺህ ከሚቆጠሩ ተወዳዳሪዎች መካከል ኪዩቢክን እንዲመረጥ አድርጎታል።
«በሚገርም ሁኔታ በአብዛኛው ያሉን  ያስመረጣቸሁ የድርጅታችሁ ልብን ነው። የሚል ሃሳብ ተጥተውናል። ልብ ሲባል ቴክኖሎጂው ጥሩ ስለሆነ አይደለም። ቶሎ ስለ ተስፋፋም አይደለም። ግን ለዓለምና ለሌላም ሰዎች እንዴት ይሄ ነገር ኑሮ ያሻሽላል ብለን ስላሰብን ያንን ነው ያዩት።ለምን ባሁኑ ጊዜ ትልቁ ትኩረት «ፕሮፊት» ላይ ነው። እንዴት አድርጎ ድርጅቱ ቶሎ ገንዘብ መስራት ይችላል በሚል ነው። የኛ ግን እንደዛ ብሎ አልጀመረም። የሰው ኑሮ ማሻሻል ብለን ነው።  መጀመርያ ያየነው ነው። እና ያ ነው የኛ ልብ። ልባችን ሀገራችንም ሆነ ዓለምን  ማሻሻል አለብን ብለን ነው ይህን ድርጅት ለማቋቋም ያበቃን።» 

እድገት ቆሻሻ ሂደት ሊሆን አይገባም» የሚል መርህ ያለው ይህ የቴክኖሎጅ ኩባንያ፤ ከጠቀሜታው አንፃር በሸላሚ ድርጅቱ ብቻ ሳይሆን በብዙ አካላት ዘንድ አወንታዊ መልክ እንደሚታይ ገልፀዋል። ሽልማቱ ደግሞ ከተለያዩ አጋሮች ጋር ለመስራት ተጨማሪ ዕድል ከፍቶላቸዋል።በዓለም አቀፉ የህፃናት አድን ድርጅት በእንግሊዝኛው ምህፃሩ ዩኒሴፍ ውስጥ የዓለም አቀፍ የኢኖቬሽን መርሀ ግብር ሀላፊ በመሆን የሰሩት አቶ ቅዱስ፤ በስራቸው ምክንያት በአፍሪቃ፣ በእስያ እና በደቡብ አሜሪካ በሚገኙ በበርካታ ታዳጊ ሀገራት ተዘዋውረዋል።በእነዚህ ታዳጊ ሀገራት የተመለከቷቸው ችግሮች እና ችግሮቹን በመፍታት ረገድ ያገኙት ተሞክሮ  ታዲያ፤ እሳቸው እንደሚሉት ይህንን የቴክኖሎጅ ኩባንያ የማቋቋም ሀሳብ እንዲያድርባቸው ምክንያት ሆኗቸዋል።«ከ40 በላይ ሀገራት እሰራ ነበር። አፍሪካ ውስጥም ኤዢያ ውስጥም  ላቲን አሜሪካ ውስጥም። እና አንድ ችግር ያየሁት በነዚህ ሀገሮች ከተሞች ቶሎ ያድጉ ነበር።በዚያ ወቅት የቆሻሻ ለቀማ ችግር ያጋጥማቸዋል። ህዝባቸው ደህና ዓይነት አኗኗር አይኖርም። ሌላው  የነበራቸው ችግር ጥሩ ቤት ውስጥ ለመኖር በጣም ዋጋው ከፍተኛ ስለነበረ ጥሩ አኗኗር አልነበራቸውም። ከዚያ በተጨማሪ ደግሞ «ክላይሜት ቼንጅ» ትልቅ «ፎከስ» ነበር ዩኒሴፍ ውስጥ። ትልቅ የክላይሜት ቼንጅ «ኮንቢተሮች» ደግሞ ከተማዎች ናቸው።ምክንያቱም የቤት መሣሪያዎች እንደ ስሚንቶ ብሉኬት ያሉ ነገሮች በጣም በጣም አከባቢን ይበክሉ ነበር።እና ኢሄን ስናይ እንዴት አድርገን ልንዋጋ ንችላለን የሚል ሀሳብ ነው። አይቮሪኮስት ውስጥ አንድ ፕሮግራም ያቋቋምነው።» 

Kenia Äthiopien Start-Up l Kubik Technology l CEO und Mitgründer Kidus Asfaw
ምስል privat

በማለት ከገለፁ በኋላ በዚህ መርሀግብር ፋብሪካ በመገንባት እና ከፕላስቲክ የግንባታ ቁሳቁስ በመስራት 300 ትምህርት ቤቶች መሰራታቸውን አመልክተዋል። ከዚህ በተጨማሪ የመኖሪያ ቤቶችን ለመስራት እሳቸው የሚሰሩበት ድርጅት ዩኒሴፍ ቢፈልግም፤በዘርፉ አቅም ያላቸው ድርጅቶች አለመኖራቸውን ገልፀዋል። ይህ ቴክኖሎጅ ችግር ፈቺነቱን እና ለህብረተሰቡ የሚሰጠው ጥቅም  ከፍተኛ መሆኑን አቶ ቅዱስ በዚህ መንገድ ቢገነዘቡም፤ በወቅቱ በዚህ ቴክኖሎጅ ላይ ገፍተው የሚሰሩ አቅም ያላቸው ድርጅቶች አለመኖራቸውን ሲመለከቱ ግን ዩኒሴፍን ለቀው ራሳቸው ድርጅት በማቋቋም ስራውን መቀጠላቸውን ገልፀዋል። በዚህ መንገድ የተቋቋመው ኪዩቢክ ባለፉት ሁለት ዓመታት ወደ ስራ ለመግባት በዝግጅት ላይ የቆየ ሲሆን በቅርቡ ግን ፤ ምርት እና አገልግሎቱን ለተጠቃሚው ለማድረስ ለጊዜው እስከ አስር ቤቶችን መገንባት ሚያስችል በቀን ወደ 45 ሺህ ኪሎ የሚሆን የፕላስቲክ ቆሻሻን ወደ ምርት መለወጥ የሚችል ፋብሪካ በአዲስ አበባ መክፈታቸውን ተናግረዋል።

Kenia Äthiopien Start-Up l Kubik Technology l CEO und Mitgründer Kidus Asfaw
አቶ ቅዱስ አስፋው ከስራ ባልደረቦቻቸው ጋር ምስል privat

በጎርጎሪያኑ 2022 ዓ/ም ኪዩቢክ በአዳማ የኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ቦታ ለመከራየት እና  የፕላስቲክ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። በዚህም ተቋሙ በዓመት 10,000 ቶን የፕላስቲክ ቆሻሻን  በማቀነባበር በአነስተኛ ካርቦን ልህቀት ዝቅተኛ ዋጋ ያላቸውን የግንባታ ቁሳቁሶችን ያመርታል ተብሎ ይጠበቃል።ለወደፊቱም ቴክኖሎጅውን በተለያዩ የአፍሪቃ ሀገራት የማስፋፋት ዕቅድ ይዘዋል።ትውልድ እና እድገታቸው አዲስ አበባ የሆኑት አቶ ቅዱስ፤ በባዮሜዲካል እና ኤለክትሪክ ምህንድስና በአሜሪካን ሀገር ዱኬ እና ፕሪስተን ዩንቨርሲቲ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል። አክሴቼር፣ጎግል፣ ዓለም ባንክ እና ዩኒሴፍን ጨምሮ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ሰርተዋል። ይሁን እንጅ ለእሳቸው የበለጠ ጠቃሚ እና አስፈላጊው ነገር የስራ ልምዳቸውን  እና ዕውቀታቸውን ለሀገራቸው ማዋላቸው ነው።ለዚህም የወላጆቻቸው ምክር አስተዋፅኦ ማድረጉን ገልጸዋል።
«ወላጆቼ የሰጡን ገንዘብ ነው ።«ወላጆቼ ያላቸውን ገንዘብ በትምህርት ቤቴ ላይ ነው ያጠፉት። በወንድሞቼ ትህርት ቤት ላይ ነው ያጠፉት። ያ ብዙ ዕድል ሰጥቶናል።ግን በዚህ ዕድል በቃ ሄዳችሁ አሜሪካ ወይም ሌላ ቦታ ሄዳችሁ ኑሩ አላሉም። ያሉን ሂዱ ተማሩ ዕውቀት ያዙ ግን ሀራችሁን አትርሱ ነው ያሉን።» ብለዋል አቶ ቅዱስ አስፋው። 

Kenia Äthiopien Start-Up l Kubik Technology l CEO und Mitgründer Kidus Asfaw
የኪዩቢክ ተባባሪ መስራች እና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቅዱስ አስፋው ምስል privat

ሙሉ ዝግጅቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።

ፀሀይ ጫኔ
ነጋሽ መሀመድ