1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቃለ-ምልልስ ከዮናታን ተስፋዬ ጋር

ሰኞ፣ የካቲት 26 2010

ከታህሳስ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ የቆዩት የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ዛሬ ዝዋይ ከሚገኘው ማረሚያ ቤት ተለቅቀዋል። አቶ ዮናታን ከእስር ከተፈቱ በኋላ ለዶይቼ ቬለ እንደተናገሩት ዛሬ የተፈቱት ድንገት ሳያስቡት ነው።

https://p.dw.com/p/2tk06
Äthiopien, Yonatan Tesfaye - Blue Party
ምስል Blue Party

ቃለ-ምልልስ ከዮናታን ተስፋዬ ጋር

የእስር ጊዜያቸውን ለመጨረስ አንድ ወር ከ18 ቀን ብቻ ይቀራቸው እንደነበር የተናገሩት አቶ ዮናታን ዛሬ በድንገት መለቀቃቸውን ገልጸዋል። ወደ አዲስ አበባ የሚወስደው መንገድ በተዘጋበት ቀን ከእስር በመውጣታቸው መቸገራቸውን አስረድተዋል። ቀደም ሲል በርካታ እሥረኞች በተለቀቁበት ወቅት የይቅርታ ደብዳቤ እንዲፈርሙ ቀርቦላቸው እንደነበር አስታውሰው አልፈርምም በማለታቸው እዚያው እንዲቆዩ መደረጉን ተናግረዋል።

ወጣቱ ፖለቲከኛ የታሰሩት ከሶስት አመት ገደማ በፊት የኦሮሞ ተቃውሞ በተቀሰቀሰ በወሩ አካባቢ ነበር። በግል የፌስቡክ ገጻቸው በፃፏቸው አስተያየቶች ሽብርን የማበረታታት ክስ ቀርቦባቸው የነበረው አቶ ዮናታን በሽብርተኝነት የተፈረጀው የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦነግ) አባል ናቸው በሚልም ተወንጅለዋል። 
የቀረበባቸውን ውንጀላዎች ተቃውመው በፍርድ ቤት ሲከራከሩ የነበሩት ፖለቲከኛው በወቅቱ በእስር ላይ ይገኙ የነበሩትን የኦሮሞ ፌድራሊስት ኮንግረስ አመራሮች ዶ/ር መረራ ጉዲና እና አቶ በቀለ ገርባ እንዲሁም ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን በመከላከያ ምሥክርነት ጠርተውም ነበር።

Yonatan Tesfaye Äthiopien
ምስል DW/Y.Geberegziabehr

አወዛጋቢውን የጸረ-ሽብር አዋጅ ተላልፈዋል በሚል የቀረበባቸውን ክስ ሲመለከት የቆየው የከፍተኛው ፍርድ ቤት አቶ ዮናታን በፌስቡክ ገጻቸው ያሰፈሯቸው አስተያየቶች በመንግሥት ሽብርተኛ ከተባሉ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ባይኖራቸውም ኹከት የመቀስቀስ አቅም አላቸው ማለቱ አይዘነጋም። የጥፋተኝነት ውሳኔ ያስተላለፈው ፍርድ ቤቱ ስድስት ዓመት ከስድስት ወር እንደፈረደባቸውም ይታወሳል። አቶ ዮናታን በውሳኔው ላይ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ያሉ ሲሆን ፍርድ ቤቱም ክሳቸውን ከሽብር ወደ መደበኛ የወንጀል ክስ ቀይሮ የእስር ጊዜያቸውን ወደ ሶስት ዓመት ከስድስት ወር ቀንሶላቸዋል።

አቶ ዮናታን ከእስር ከተፈቱ በኋላ ከዝዋይ ወደ አዲስ አበባ እየተጓዙ ባለበት ወቅት በስልክ ለዶይቼ ቬለ የሰጡትን ሙሉ ቃለ ምልልስ የድምጽ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።

ተስፋለም ወልደየስ

አርያም ተክሌ