ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ኪንሻሳ ገቡ
ማክሰኞ፣ ጥር 23 2015ማስታወቂያ
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ-ክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ሁለት የአፍሪቃ ሐገራትን ለመጎብኘት ዛሬ ኪንሻሳ-ኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ገቡ።ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ለአምስተኛ ጊዜ ወደ አፍሪቃ ባደረጉት ጉዞ ከኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ በተጨማሪ ደቡብ ሱዳንንም ይጎበኛሉ። ፍራንሲስ ከሮም ከመነሳታቸዉ በፊት ከርዕሰ-መንበራቸዉ ቫቲካን የወጣዉ መግለጫ እንዳመለከተዉ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ሁለቱን በጦርነትና ግጭት ክፉኛ የተመሰቃቀሉ ሐገራትን የሚጎበኙት ለሰላምና ለሕዝብ ደሕንነት ለመጸለይ ነዉ። አንድ የሮማ ካቶሊካዊት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ደቡብ ሱዳንን ሲጎበኝ ያሁኑ የመጀመሪያዉ ይሆናል። ለኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ደግሞ እንደ ግሪጎሪያኑ አቆጣጠር ከ1985 ወዲህ የመጀመሪያዉ ነዉ። አንድ መቶ ሚሊዮን ከሚገመተዉ ከሰፊዋ አፍሪቃዊት ሐገር ሕዝብ 40 በመቶዉ የካቶሊክ ክርስትና እምነት ተከታይ ነዉ።የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱን ጸሎትና ቡራኬ ለመቀበል ከርዕሰ ከተማይቱ ነዋሪ በተጨማሪ በብዙ ሺሕ የሚቆጠር አማኝ ከያለበት ወደ ኪንሻሳ ሲጎርፍ ነዉ የሰነበተዉ። ፍራንሲስ በሁለቱ ሐገራት የሚደረጉት ጉብኝት 6 ቀን ይፈጃል።
ነጋሽ መሐመድ
አዜብ ታደሰ