ርዕሠ ብሔር ሳህለወርቅ ዘውዴ ያደረጉት ንግግር
ሰኞ፣ መስከረም 24 2014የሀገርን ህልውና እና የህዝባችን አንድነት አደጋ ላይ የሚጥሉ እንደዚሁም ለቀውስ ምክንያት ሆነው የኖሩ ችግሮች በብሔራዊ መግባባት ሊፈቱ ይገባል ሲሉ ርዕሠ ብሔር ሳህለወርቅ ዘውዴ በ6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መስራች ጉባኤ ላይ ተናገሩ።
የምንመኘው ብሄራዊ መግባባት ይፈጠር ዘንድም ታጋሽነት፣ መተማመን፣ መመካከር፣ ህብረትና አንድነት እና የክርክር ባህሎችን ማዳበር ይኖርብናልም ብለዋል።
በሌላ በኩል ፍትሕ እንና ተጠያቂነትን ማስፈን ፣ የተጎዱትን መካስ፣ ማህበራዊ ፍትህ ማስፈንም ይገባል ብለዋል ርዕሠ ብሔሯ። በአመፅ እና በጠመንጃ ትግል አልያም ንፁሃንን በማሸበር የሚገኝ ስልጣን ከዚህ በኋላ በኢትዮጵያ ምድር የማይፈጠሩ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፣
ስልጣን ሰጭውም ሆና ነሺው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፣ ስለሆነም የሀገራችን ፖለቲከኞች እና የፖለቲካ ፓርቲዎች ለዴሞክራሲው መንገድ በሚካሄድ ህጋዊ ምርጫ ብቻ በመሳተፍ ህዝባችሁንና አገራችሁን የምታገለግሉበት ሰላማዊ የፉክክር መድረክን ብቻ እንድትመርጡ ለማሳሰብ እወዳለሁ ብለዋል ርዕሠ ብሔር ሳህለ ወርቅ ዘውዴ።
ኢትዮጵያ የ 90 ዓመታት የሕዝብ ውክልና ልምድ ያላት አገር ናት ያሉት ርዕሠ ብሔር ሳሕለ ወርቅ ዘውዴ ወደድንም ጠላንም ተለዋጭ አገር የለንም ያለን አማራጭ ተቻችሎ መኖር ነው ብለዋል። ኢትዮጵያውያን አሁንም ሆነ ወደፊት በሀገራችን ሉዓላዊበት እና ብሔራዊ ጥቅም ከማንም ጋር አንደራደርም ብለዋል።
ሰለሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሰ