ሕወሓት የኢህአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ አይሳተፍም
ረቡዕ፣ ኅዳር 10 2012ማስታወቂያ
የህወሓት ማእከላይ ኮሚቴ አባላት ነገ በሚጀመረው የኢህአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ እንደማይሳተፉ የህወሓት ፅሕፈት ቤት ገለፀ። ህወሓት በይፋዊ የፌስቡክ ገፁ በኩል ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው የኢህአዴግ ውኅደት በግንባሩ ሥራ አስፈፃሚ ደረጃ ይሁን ምክር ቤት ስብሰባ ሊወሰን የማይችል መሆኑን ጠቅሶ አባላቱ ነገ በሚጀምረው የኢሕአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ እንደማይሳተፉ ዐስታውቋል።
አራቱ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች እያንዳንዳቸው 45 ተወካዮች የሚያሳትፉበት የኢህአዴግ ምክር ቤት ከነገ ጀምሮ ስብሰባ እንደሚያካሂድ ግንባሩ በዛሬው ዕለት ገልጿል። «የህወሓት እጣ ፈንታ ሊወሰን የሚችለው በየደጃው ውይይት ከተደረገበት በኋላ በህወሓት ጉባኤ ብቻ በመሆኑ በአሁኑ ሰአት ስብሰባ ላይ ለመሳተፍ የማንችል መኾኑን እናሳውቃለን» ይላል የህወሓት መግለጫ። ከኢሕአዴግ ምክር ቤት 180 አባላት መካከል 45ቱ የህውሓት አባላት ናቸው።
ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በግንባሩ ውኅደት ዙርያ የቀረበው የጥናት ውጤትን በአብላጫ ድምፅ ማፅደቁ ይታወሳል። ጉዳዩ በግንባሩ ምክር ቤት ደረጃ እንደሚታይም ተገልፆ ነበር።
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
ማንተፍቶት ስለሺ