1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ልጆቻቸው ትግራይ ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ወላጆች ድምጽ

ዓርብ፣ ሐምሌ 16 2013

ልጆቻቸው ትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች የሚማሩ ወላጆች እና ቤተሰቦች ዛሬ ጠዋት በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ጽሕፈት ቤት ቢሮ በር ደጃፍ ጥያቄያቸውን አቀረቡ።

https://p.dw.com/p/3xwd1
Äthiopien | Demonstration von Eltern in Addis Abeba
ምስል Solomon Muchie/DW

ከተመድ ጽሕፈት ቤት ደጃፍ ተሰልፈዋል

ልጆቻቸው ትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች የሚማሩ በርከት ያሉ ወላጆች እና ቤተሰቦች ዛሬ ጠዋት በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ጽሕፈት ቤት ቢሮ በር ላይ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል። ወላጆቹ «ልጆቻችን እስክሪብቶ እና ደብተር ብቻ ይዘው ለመማር ነው የሄዱት፣ አስመልሱልን» የሚሉ ጥያቄዎችን በለቅሶ እና እንባ በታጀበ ድምፅ አሰምተዋል። ጥያቄ አቅራቢዎቹ ትግራይ ውስጥ የሚገኙት ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎቹን ለመመለስ የነዳጅ ፍጆታ እንደሌላቸው መናገራቸውን የተባበሩት መንግሥታት ተነግሮናል ብለዋል። ከዚህ መነሻ የነዳጅ ፍጆታውን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ለመሸፈን ተስማምቶ ሚኒስቴሩ በተባበሩት መንግሥታት በኩል ሁለት ቦቴ ነዳጅ ማቅረቡን እና 63 አውቶቡሶች ማዘጋጀቱን እንደገለፀላቸው ቅሬታ አቅራቢዎቹ ተናግረዋል። ሆኖም ከእሁድ እስከ ማክሰኞ ይመለሳሉ የተባሉት ተማሪዎች መውጣት ስላልቻሉ ለጥያቄ ዛሬ መውጣታቸውንም ወላጆች ተናግረዋል። በጉዳዩ ላይ ከሚመለከታቸው ሁሉ መረጃ ለማግኘት ያደረግኩት ተደጋጋሚ ጥረት ለጊዜው አልተሳካም።

ሰሎሞን ሙጬ

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ