ለ16ኛ ቀን ዛሬም የፖለቲከኞቹ የረሃብ አድማ ቀጥሏል ተባለ
ዓርብ፣ የካቲት 5 2013ማስታወቂያ
የረሐብ አድማ ላይ ይገኛሉ የተባሉት አቶ ጃዋር መሐመድ፣ አቶ በቀለ ገርባ እና ሌሎችም እስረኞች በከፍተኛ ሁኔታ መዳከማቸውን ከጠበቆቻቸው አንዱ ለዶይቸ ቬለ ተናገሩ። በጠያቂዎቻቸው እና በሐኪሞቻቸው የረሐብ አድማቸውን አቊመው ምግብ እንዲወስዱ ቢጠየቊም ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውም ተዘግቧል። ከዚህ ቀደም ወደ ህክምና ተወስደው የነበሩት አምስት የረሃብ አድመኞች ዛሬ ወጥተው ወደ ማረሚያ ቤቱ መወሰዳቸውንም የተከሳሾች ቤተሰቦች ተናግረዋል።
ጥር 20 ቀን 2013 ዓ.ም. በአራት አስረኞች ተጀምሯል የተባለው የረሃብ አድማው ዛሬም ለ16ኛ ቀን መቀጠሉን ቤተሰቦቻቸውና ጠበቆች ለዶይቼ ቬለ ገለጡ። በአቶ ጃዋር መሐመድ፣ አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ሃምዛ አዳነ እና አቶ ሸምሰዲን ጠሃ ተጀምሮ በኋላም በሌሎች በመዝገቡ በተጠቀሱ ተከሳሾችም ቀጥሏል የተባለው የረሃብ አድማ ገሚሶቹን ለሐኪም የዳረገ ሌሎችንም ያዳከመ መሆኑ ተነግሯል። ከዚህ ቀደም ወደ ህክምና ተወስደው የነበሩት አምስት የረሃብ አድመኞች ዛሬ ወጥተው ወደ ማረሚያ ቤቱ መወሰዳቸውን የገለጡት የተከሳሾች ቤተሰቦች ነገሩ አሳሳቢም ነው ሲሉ ገልጸውታል።
ሥዩም ጌቱ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ