በትግራይ የተጠራ ጉባኤ
ሰኞ፣ ነሐሴ 20 2011 የኢትዮጵያን ህገ መንግስት እና ሀገሪቱ የምትከተለውን ፌደራላዊ ስርዓቱን የማዳን ተልዕኮ ያነገበ አገር አቀፍ መድረክ ዛሬ በትግራይ ተጀመረ። መድረኩ የተዘጋጀው በትግራይ ክልል መንግስት ነው። “ህገ-መንግስትና ሕብረ-ብሔራዊ ፌደራላዊ ስርዓትን የማዳን አገር አቀፍ መድረክ” በሚል መሪ ሐሳብ የተጠራው ጉባኤ ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት ይቆያል። በኢትዮጵያ ህገ መንግስት እና ፌደራል ስርዓት ላይ የመወያያ ፅሁፎች እየቀረቡበት በሚገኘው በዚህ መድረክ ይህንኑ ጉዳይ የተመለከቱ ሰፊ ውይይቶች እንደሚደረጉ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
የዛሬውን መርኃ ግብር በንግግር የከፈቱት የትግራይ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል “ኢትዮጵያ በአስቸጋሪ እና ፈታኝ ሁኔታ ላይ” መሆንዋን በመጥቀስ “በፌደራላዊ ሕገ መንግስታዊ አካሄድ ሀገሪቱ ከከፋ ሁኔታ መታደግ ይገባል” ብለዋል፡፡በኢትዮጵያ አሁን የሚታዩት ችግሮች መንስኤ ሕገ መንግሥቱን አለማክበር እና የሕግ የበላይነትን አለማረጋገጥ ነው ሲሉም ተናግረዋል።ዶክተር ደብረ ጽዮን በሃገሪቱ የብሔር ግጭቶች እና ማንነት ላይ ያተኮሩ ጥቃቶች የተባባሱት ሃገሪቱ በፌደራል ስርዓት በመመራትዋ እንዳይደለ ይልቁንም ምክንያቱ ሕግን ማስከበር አለመቻል መሆኑን ገልጸዋል። ነገም በሚቀጥለው በዚህ ውይይት ላይ በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሕገ መንግስት እና ፌደራል ስርዓት ምሁራን፣ የተለያዩ ብሄረሰብ ተወካዮች እንዲሁም የትግራይ ክልል መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ሌሎች ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
ኂሩት መለሰ
ተስፋለም ወልደየስ