6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ በድሬደዋ
ሰኞ፣ ሰኔ 14 2013ማስታወቂያ
6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ በድሬደዋ አስተዳደር እና በምስራቅ ሀረርጌ ዞን ስር ባሉ አካባቢዎች በጥሩ ሁኔታ ሲካሄድ ውሏል፡፡ ዐሥር የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሁለት የግል እጩ ተወዳዳሪዎች በተሳፉበት የድሬደዋ ምርጫ ላይ በመራጭነት የተሳተፉ የድሬደዋ ነዋሪዎች ምርጫው ጥሩ መሆኑን ለዶይአ ቬለ በሰጡት አስተያየት ገልፀዋል፡፡
በአንዳንድ የምርጫ ጣቢያዎች ላይ ከታየው መዘግየት ባለፈ በብዙ ምርጫ ጣቢያዎች ምርጫው በሰላማዊ መንገድ እየተካሄደ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በምርጫው ተፎከካሪ ፓርቲ የሆነው የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ /ኢዜማ ድሬደዋ ቅርንጫፍ አስተባባሪ አቶ ዮናስ በትሩ ናቸው፡፡
የእናት ፓርቲ ድሬደዋ ተወካይ አቶ ናትናኤል ስናማው በበኩላቸው ህዝቡ በነፃነት መምረጥ መቻሉን መመልከታቸውን አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል ምርጫው በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሀረርጌ ዞን ስር ባሉ አካባቢዎች በተዘጋጁ ከሁለት ሺህ በላይ ምርጫ ጣቢያዎች ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ መካሄዱን በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምስራቅ ሀረርጌ ዞን አስተባባሪ አቶ ጌታቸው ሚጀና ለዶይቸ ቬለ (DW) በስልክ ተናግረዋል፡፡
መሳይ ተክሉ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ
ኂሩት መለሰ