490 ኢትዮጵያውያን ከየመን ወጡ
ሐሙስ፣ መጋቢት 22 2008የ25 አመቱ ወጣት አሊ የመን ውስጥ ከሚተዳደርበት የጫት ንግድ ሥራ ታግቶ ለማስፈታት ሳዑዲ አረቢያ የሚኖሩ ቤተሰቦቹ 10,000የሪያል (2,700 ዶላር) ከፍለዋል። አሊ ከታገበት ሲፈታ ራሱን እንደ እድለኛ ቆጥሯል።
«አጋቾቹ የወንዶችን አይን በቢላ ሲወጡ ተመልክተናል።ከአንዳንዶቹ ጀርባ ላይ ፕላስቲክ ያቀልጡባቸዋል፤አንድ ወጣት ክፉኛ በመደብደቡ ምክንያት የደረቱ አጥንቶች እና እጁ ተሰባብረዋል።» ሲል በእገታ በቆየበት ጊዜ የተመለከተውን ዘግናኝ ድርጊት የሚያስታውሰው አሊ በዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት አማካኝነት በጦርነት ከታመሰችው የመን ከወጡ 490 ኢትዮጵያውያን መካከል አንዱ ነው።
በዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት የክትትል እና ኢቫሉዌሽን ባለሙያ የሆኑት አቶ አብርሐም ታምራት በየመ የሚገኙ ስደተኞች ሲታገቱ ግርፋት፤እንግልት እንደሚፈጸምባቸው ተናግረዋል። በደረሰባቸው ስቃይ የሞቱ እንደሚገኙም ባለሙያው ተናግረዋል። ስደተኞቹ ሲታገቱ በኢትዮጵያ አሊያም በሳዑዲ አረቢያ ከሚገኙ ቤተሰቦቻቸው ገንዘብ እንዲልኩ ተደውሎ ይነገራቸው። አቶ አብርሐም «እስከሶስት ጊዜ የላኩ ቤተሰቦች መኖራቸውን አረጋግጠናል» ይላሉ።
በየመን ያለው ነባራዊ ሁኔታ ለዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት ሰራተኞች ጭምር አስጊ መሆኑን የጠቆሙት አቶ አብርሐምታምራት ከየመን እና የሳዑዲ አረቢያ መንግስታት ጋር በመተባበር ስደተኞቹ መውጣታቸውን ተናግረዋል። ድርጅቱ ከየመን ሖዲዳህ የባህር ወደብ ወደ ጅቡቲ ከዛም በአውቶቡስ ወደ ኢትዮጵያ 490 ስደተኞችን ማጓጓዙን ያረጋገጡት አቶ አብርሐም «በቀጣይ ቅዳሜ እና እሁድ ደግሞ 250 ሰዎችን ለመመለስ እንቅስቃሴ ላይ እንገኛለን ሲሉ ተናግረዋል። ድርጅቱ በየመን ከሚገኙ ስደተኞች መካከል 1,212ስደተኞችን ለመመለስ አቅዷል።
በተባበሩት መንግስታት ድርጅር የስደተኞች ኮሚሽን መረጃ መሰረት በጎርጎሮሳዊው 2015 ዓ.ም ብቻ ከ92,000 በላይ ስደተኞች ወደ የመን ተጉዘዋል። ከእነዚህ መካከል ደግሞ 89%ኢትዮጵያውያን ሳይሆኑ እንደማይቀር ኮሚሽኑ ጨምሮ አስታውቋል። አቶ አብርሐም ታምራት ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ስደተኞች የሚሰማሩባቸውን የስራ ዘርፎች ለማመቻቸት ተቋማቸው ጥረት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
እሸቴ በቀለ
አርያም ተክሌ