128ኛው የአድዋ ድል በዓል በአዲስ አበባ ተከበረ
ቅዳሜ፣ የካቲት 23 2016128 ኛው ዓመት የዓድዋ ድል መታሰቢያ ክብረ በዓል በአዲስ አበባ በቅርቡ በተመረቀው የዓድዋ ሙዚየም ውስጥ በመንግሥት ደረጃ ተከበረ።
ለወትሮው ከሁሉም የከተማዋ አቅጣጫ እና ከሀገሪቱ እየመጣ ፒያሳ ምኒልክ አደባባይ እና በዙሪያእ በዓሉን ያከብር የነበረው ብዙ ቁጥር የነበረው ሕዝብ በዚህኛው ዓመት በሥፍራው በዓሉን እንዳያከብር በፀጥታ አካላት ክልከላ ተደርጎበታል።
መንግሥት በዓሉን በመከላከያ ሠራዊት አዘጋጅነት በላቀ ሁኔታ ማክበሩን ሲገልጽ ፤ ክብረ በዓሉን እንደከዚህ ቀደሙ በለመደው ሁኔታ ማክበር ባለመቻሉ ማዘኑን ገልጿል።
አከባበሩ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ ውዝግብ ያልተለየው የዓድዋ ድል ፤ በመላው ዓለም በነፃነት ወዳጅ የሰው ልጆች ሁሉ በክብር የሚወደስ ነው።
ከዛሬው በዓል አከባበር ጋር ተያይዞ ጋዜጠኞችን ጨምሮ ሌሎች ሰዎች ስለመታሰራቸው ተሰምቷል።
የአድዋ ድል በዓል አከባበር ዉዝግብና የህዝብ አስተያየት
ኢትዮጵያውያን ከ128 ዓመታት በፊት ቅኝ ሊገዛቸው የመጣውን የጣልያን ወራሪ ኃይል ሰዓታት እንኳን ባልፈጀ ጦርነት በአንድነት ያሸነፉበት ታላቁ የዓድዋ ድል ዛሬ የካቲት 23 ቀን በመንግሥት ደረጃ በዓድዋ ሙዚየም ተከብሯል።
በአሁኑ ወቅት የአንድነት ፈተና ውስጥ የወደቀችው ኢትዮጵያ፣ በጦርነት የምትታመሰው የዓድዋ ድል ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ ፣ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ በበዓሉ አከባበር ሥፍራ ፣ በድሉ መሪዎች ፣ በበዓሉ ላይ ተለብሰው፣ ተይዘው በሚወጡ አርማዎች ፣ በሚታተሙ የድሉ ማድመቂያ ቁሶች ልዩነቶች ጎልተው እየተስተዋሉ ይታያሉ።
በዛሬው በዓል ላይ ለወትሮው በተለይ ፒያሳ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስትያን ሥር በሚገኘው ምኒልክ አደባባይ በብዙ ሺህ ቁጥር ተገኝቶ በዓሉን በሕብር ያደምቅ የነበረው ሕዝብ በፀጥታ ኃይላት በአራቱም አቅጣጫ ወደ አደባባዩ እንዳይገባ ክልከላ ተደርጎበት በዓሉን ማክበር ሳይችል ቀርቷል። ሁኔታውን የታዘቡ ሰዎችም ይህንኑ አረጋግጠዋል።
ክብረ በዓሉ መንግሥት እንዳለው በላቀ ድምቀት ፣ በተሻለ ደረጃ ተከብሯል። በዓሉን ፒያሳ ላይ ተገኝተው መታደም ያልቻሉ ነዋሪዎች ግን በሕዝብ ዘንድ እስካሁን ካዩት ሁሉ ከፍተኛ የስሜት መፋዘዝ የታየበት በዓል ይሄኛው ነው።
ከዚህ በፊት በምኒልክ ሃውልት እና አደባባይ ዙሪያ በዓሉ ሲከበር የሕዝብ ማእበል ይታይ ነበር ። ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት ለምን አይገኙም? የሚለው ቅሬታም ይነሳ ነበር። ዛሬ የሆነው ግን በተቃራኒው ነው። የመንግሥት ባለሥልጣናትና ጥሪ የተደረገላቸው በበዓሉ ላይ ሲታደሙ የበዓሉ አክባሪ ሰው ግን ያንን ማድረግ አልቻለም።
ባለፈው ዓመት 127 ኛው የዓድዋ ድል ክብረ በዓል በብሔራዊ ደረጃ ሲከበር በበዓሉ አክባሪዎች እና በሥነ ሥርዓት አስከባሪ ፖሊሶች መካከል ፍጥጫ ተፈጥሮ ፖሊሶችም የበዓሉን ታዳሚ ለመበተን አስለቃሽ ጢስ ሲተኩሱና ድብደባ ሲፈጽሙ ታይተው ነበር። በዓሉም በምኒልክ አደባባይ ፣ በዓድዋ ድልድይ እና በመስቀል አደባባይ ተከብሮ ነበር። በዚህኛው ዓመት ግን በዓሉ አንድ ሥፍራ ላይ ተከብራል።
ኢሰመኮ በአደዋ በዓል ሰው የገደሉ እንዲጠየቁ አሳሰበ
ከዚሁ የበዓሉ አከባበር ጋር በተያያዘ "አድዋ ሩጫ" በሚል ተዘጋጅቶ የነበረ እና የተሰረዘ የሩጫ ውድድር አዘጋጅ ጋዜጠኞች ዛሬ ማለዳ መታሰራቸው ተሰምቷል።
ዶይቼ ቬለን ጨምሮ ሌሎች የውጭ መገናኛ ብዙኃን የዘንድሮው የዓድዋ ድል መታሰቢያ ላይ ተገኝተው መዘገብ የሚያስችላቸውን የመግቢያ ካርድ ባለማግኘታቸው በሥፍራው ላይ መገኘት አልቻልንም።
ሰለሞን ሙጬ
ታምራት ዲንሳ