ጫማ የሚያመርቱት ጓደኛሞች
ዓርብ፣ ሚያዝያ 7 2008
አዛርያ መንግሥቱ እና ጆአድ ብሬይ ከልጅነታቸው ጀምሮ የሚተዋወቁ ሁለት ጓደኛሞች ናቸው። ከአምስት ዓመት በፊት ለሌላ ድርጅት ሳይሆን የራሳቸው ንግድ ከፍተው ለመስራት ወሰኑ። በዚሁ ውሳኔያቸው መሠረትም ኢትዮጵያ ውስጥ ጫማ ማምረት ጀመሩ። የንግድ ምልክቱንም ኤንዚ ( ENZI) የሚል መጠሪያ ሰጡት።
አዛርያ የተወለደው በዩናይትድ ስቴትስ ሲሆን ያደገው በኬንያ መዲና ናይሮቢ ነው። ከቅርብ ዓመታት አንስቶ ደግሞ መኖሪያ እና ስራውን በአዲስ አበባ አድርጓል። ሌላው የኤንዚ መስራች ጆአድ ተወልዶ ያደገው ኬንያ ውስጥ ነው። በብሪታንያ ፤ ለንደን ዮንቨርስቲ ኦፍ አርት« የፕሮዳክት ዲዛይን» ትምህርት የተከታተለው ጆአድ ዋና ትኩረቱ የጫማ አይነቶችን መቅረፅ ( ዲዛይን) ማድረግ ነበር።
አዛርያ እና ጆአድ ክርስትያን እና ሳም የሚባሉ አብረዋቸው የሚሰሩ ሸሪኮች አሏቸው። እንዲሁም እስካሁን አራት ሰራተኞች ቀጥረዋል። ኤንዚ ስራ ሲጀምር በቀን አንድ ጥንድ ጫማ እንኳን የማያመርትበት ጊዜ ነበር ይላል አዛርያ። አዲስ ንግድ ሲጀመር፤ ራሱን የቻለ ፈተናዎች ይኖሩታል። ጆአድ የገጠማቸውን ፈተና ሲያስረዳ፤ « መጀመሪያ ላይ ጫማዎቻችንን ሀገሩ ውስጥ ካሉ የጫማ ፋብሪካዎች ጋር ተባብረን ማምረት ፈልገን ነበር። ምክንያቱም መሣሪያዎቹ አልነበሩንም ። ነገር ግን በወቅቱ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት አብዛኞቹ ፋብሪካዎች የሚያመርቷቸው ጫማዎች ጥራት ዝቅተኛ ነበር።
ምርቶች በሰዓቱ አይቀርቡም፣ አንዳንዴ ለቀናት የኤሌክትሪክ ኃይል ስለሚጠፋ ጫማዎቹ እንደፈለግነው አይመረቱም። በዛ ላይ ስለ ደሞዝ አከፋፈሉ የምናውቀው ነገር አልነበረም። እነዚህ ነገሮች ከአቅማችን በላይ ሆነው ነበር። ቀደም ሲል ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የቆዳ ውጤት ጥራት ጥሩ ነው ብያለው፤ ነገር ግን አንዳንዴ ቆዳው ከየት እንደሚመጣ ስለማናውቅ አንድ አይነት ጥራት ያለው ቆዳ ማግኘቱ አስቸጋሪ ነበር። እና መጀመሪያ ላይ እነዚህን መሰል ፈተናዎች ነበሩብን።»
ኤንዚ በአሁኑ ወቅት እስከ ሰባት በእጅ የተሰሩ ጥንድ ጫማዎች በቀን ያመርታል። ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚሸጠው የጫማ ብዛት ይልቅ ለውጭ ገበያ የሚያቀርበውም ይበልጣል። ለመሆኑ ደንበኞቹ እነማን ናቸው? መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ላይ ስላደረጉ ሁለት ጫማ አምራች ጓደኛሞች ሙሉ ዘገባ በድምፅ ያገኛሉ።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ