ጥላቻ አዘል መልክቶች ቁጥጥር ሊደረግባቸዉ ይገባል
ዓርብ፣ መስከረም 11 2011በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የሚታየዉን የቡድን ጥቃትና አመፅን መንግሥት ሊያስቆም ይገባል ሲል ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት «አምነስቲ ኢንተርናሽናል» ገለፀ። የአምስንቲ ኢንተርናሽናል የሠብአዊ መብት አጥኚ ዛሬ ለ«DW» እንደተናገሩት፤ ሰዎች መብታቸዉን አልፈዉ የሰዉን መብትን በሚነኩበት ጊዜ መንግሥት ርምጃ ካልወሰደ ከሆደ ሰፊነት አልፎ ግዴታዉን አለመወጣም። በተለይ በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ከአገር ዉስጥም ሆነ ከዉጭ የሚሰራጩ ጥላቻ አዘል መልክቶችን መንግስት ሊቆጣጠራቸዉ ይገባል ብሎአል። በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች የሚሰራጭ ማንኛዉም የጥላቻ መልክት በዓለምአቀፍ ደረጃ ወደ ሕግ ማምጣት እንደሚቻልም አያይዞ ጠቅሶአል።
በቡራዩ እና በሌሎች የአዲስ አበባ ከተማ አካባቢዎች ተከስቶ የነበረዉ አመጽና ግድያ መነሻ የተጠነሰሰዉ ምናልባት ከዛሬ ሦስት አራት ዓመታት በፊት ሳይሆን እንዳልቀረ ነዋሪዎችን አነጋግሮ መረጃ እንደደረሰዉ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ለ«DW» ገልፆአል።የድርጅቱ የምሥራቅ አፍሪቃ የሰብአዊ መብት አጥኚ አቶ ፍሰሐ ተክሌ እንደሚሉት በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ጽንፍ ይዘዉ የጥላቻ መክክቶችን በሚያስተላልፉ ሰዎች ላይ መንግሥት ርምጃ መዉሰድ አለበት። በአዲስ አበባና በቡራዩ ከተማ አካባቢ ሰዎች መገደላቸዉንና መፈናቀላቸዉን በመቃወም የከተማዉ ሕዝብ ቁጣዉን ለመግለፅ አደባባይ ሲወጣ የፀጥታ ኃይላት ሰዉን ማስቆም አልነበረባቸዉም ያለዉ የሰብዓዊ መብት ተከታካሪ ድርጅቱ ፤ በሰልፉ ወቅት የተገደሉት አምስት ሰዎች አሟሟት እንዲጣራም ጠይቆአል።
ከቡራዩ የተፈናቀሉት ሰዎች ወደ ቀያቸዉ የመመለስ ስጋት ቢኖርባቸዉ የሚያስደንቅ አልደለም ያሉት አቶ ፍስሃ መንግሥት ሆደ ሰፊ ሳይሆን ሕግን ማስከበር ይኖርበታል። ሙሉ ቅንብሩን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ