የወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን
እሑድ፣ የካቲት 3 2011ማቋቋሚያ አዋጅ ከአንድ ወር በፊት በኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጸደቀውን የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽንን በሚመለከት የሚካሄደው ክርክር እንደቀጠለ ነው። አዋጁ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀረበበት ወቅት በምክር ቤቱ የትግራይ ክልል ተወካዮች ሕገ መንግሥቱን ይጻረራል ሲሉ መጽደቅ እንደሌለበት ተሟግተው ድጋፋቸውንም ነፍገውታል። የክልሉ ምክር ቤት ከ3 ሳምንት በፊት ባካሄደው ስብሰባም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያፀደቀውን ይህንኑ አወጅ እንደሚቃወም በመግለጽ እንዲስተካከል የሚጠይቅ ውሳኔ አስተላልፏል። ይህ ውሳኔም እንዲሁ ማከራከሩ እንደቀጠለ ነው። ኮሚሽኑ መቋቋሙን የሚደግፉ በኢትዮጵያ የግጭት መነሻ የሚሆኑ የወሰን እና የማንነት ጉዳዮችን በመመርመር የችግሩን መንስኤ በመጠቆም የመፍትሄ ሃሳቦችን ከመጠቆም ውጭ ሌላ ሥልጣን የለውም በማለት ህገ መንግሥቱንም አይጻረርም ሲሉ ይከራከራሉ። እነዚህ ወገኖች ይልቁንም የክልሉ ምክር ቤት ያጸደቀውን አዋጅ መቃወሙ ነው ህገ መንግሥቱን የሚጻረረው ይላሉ። የኮሚሽኑ መቋቋም ያስነሳው ውዝግብ እና አስተምህሮቱ የዛሬው እንወያይ የመነጋገሪያ ርዕስ ነው። በዚህ ርዕስ ላይ የሚወያዩ ሦስት እንግዶችን ጋብዘናል። እነርሱም ዶክተር አወል ቃሲም አሎ በለንደን ኪል ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ፤ ረዳት ፕሮፌሰር መረሳ ፀሐይ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር። አቶ እንዳልካቸው ገረመው የህገ መንግሥት እና መንግሥታዊ ጉዳዮች ህግ መምህር የነበሩ ከፌደራሊዝም ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ላይ ልዩ ልዩ ጥናታዊ ጽሁፎችን ያቀረቡ እና ጠበቃ ናቸው። ከታች የሚገኘውን የድምጽ ማዕቀፍ በመጫን ሙሉውን ውይይት ማዳመጥ ይቻላል።
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ