1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተደጋጋሚዉ ግጭት እና ቀዉስ

ረቡዕ፣ ኅዳር 26 2011

እርግጥ ነዉ የምዕራብ ኦሮሚያ፣ የበኒ ሻንጉል ግጭት ሰሞኑን፣ ጠንከር፣ ከረር ዉጤቱም መረር ብሏል። ግጭት፣ ሁከት፣ ሥርዓተ አልበኝነት ግን የሁለቱ አካባቢዎች ብቻ አይደለም። ከሰሜን ምዕራብ ወልቃይት ጠገዴ፣ ቅማንት እና ራያ፣ እስከ ምሥራቅ ጭናቅሰን፤ ከደቡብ ምዕራብ ቴፒ፣ እስከ ደቡብ ሞያሌ በግጭት እየታወኩ ነዉ።

https://p.dw.com/p/39XZm
Karte Äthiopien AM

Äthiopien konflikt und Anarchie - MP3-Stereo

ኢትዮጵያ ዉስጥ በተለያዩ አካባቢዎች የተቀሰቀሱ ግጭቶችን ለማስወገድ የፌደራል እና የክልል መንግሥታት ጠንከር ያለ እርምጃ እንደሚወስዱ እያስታወቁ ነዉ። በተለይ በበኒ ሻንጉል እና በኦሮሚያ አዋሳኝ ድንበሮች የከፋዉን ግጭት ለመግታት የፌደራሉ መንግሥት ያዘመተዉ ፀጥታ አስከባሪ ለግጭቱ ተጠያቂ ያላቸዉን ከ220 በላይ ሰዎችን አስሯል። የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ተጠጣሪዎችን የሚመረምር ቡድን ወደአካባቢዉ መላኩንም አስታዉቋል። የበኒሻንጉል ጉሙዝ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (በጉሕዴፓ) ግጭቱን ቀስቅሰዋል በሚላቸዉ ባለሥልጣናቱ ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታዉቋል። የኦሮሚያ መስተዳድር ካቢኔ በበኩሉ ሕዝቡን ለማረጋጋት እና ለግጭቱ ተጠያቂ የሚባሉትን ለሕግ ለማቅረብ የሚወሰደዉ እርምጃ ይቀጥላል ባይ ነዉ። የፖለቲካ ተንታኝ እና አቀንቃኝ ገረሱ ቱፋ እንደሚሉት ግን በመላዉ ኢትዮጵያ ሕግ እና ሥርዓትን ለማስከበር የእስካሁኑ እና የመንግሥት እርምጃ ብቻ በቂ አይደለም። 

ስብሰባ፣ ለኢትዮጵያ ባለሥልጣናት፣ በእዉቅ ሐኪም እንደታዘዘ እንክብል የጧት፤ ቀትር-ምሽት ምግባር ነዉ። መግለጫም በሽ ነዉ። ሐሙስ፣ የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ እና መግለጫ፣ ቅዳሜ የብሔራዊ ፀጥታ ምክር ቤት መግለጫ፣ ሰኞ፣ የአፋር ብሔራዊ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አብዴፓ) ስብሰባ፣ ማክሰኞ የበኒ ሻንጉል ጉሙዝ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (በጉሕዴፓ) ሥብሰባ እና መግለጫ፣ ማክሰኞ፣ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ መግለጫ ሁሉም ሠላም እና ፀጥታ ለማስፋን ቃል ይገባሉ። አዋኪዎችን ለመያዝ ይዝታሉ። ዉጤት-እስከ ትናንት።
አቶ ዴሬሳ ተረፈ የኦሮሚያ የኮሙኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ። ትናንትናዉኑ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ግጭት ቀስቅሰዋል ተብለዉ የሚጠረጠሩ ሰዎችን ጉዳይ የሚያጣራ የመርማሪዎች ቡድን ግጭት ወደተቀሰቀሰበት አካባቢ መላኩን አስታዉቋል። አቃቤ ሕግ አካባቢዉን አልጠቀሰም። ፀጥታ አስከባሪዎች ያዟቸዉ የተባሉት ሰዎች ማንነትም በግልፅ አልተነገረም። የተያዙት ግን በኒሻንጉል እና ምዕራብ ኦሮሚያ ዉስጥ እንደሆነ አቶ ዴሬሳ ገልጠዋል።
እርግጥ ነዉ የምዕራብ ኦሮሚያ፣ የበኒ ሻንጉል ግጭት ሰሞኑን፣ ጠንከር፣ ከረር ዉጤቱም መረር ብሏል። ግጭት፣ ሁከት፣ ሥርዓተ አልበኝነት ግን የሁለቱ አካባቢዎች ብቻ አይደለም። ከሰሜን ምዕራብ ወልቃይት ጠገዴ፣ ቅማንት እና ራያ፣ እስከ ምሥራቅ ጭናቅሰን፤ ከደቡብ ምዕራብ ቴፒ፣ እስከ ደቡብ ሞያሌ በግጭት እየታወኩ ነዉ።የአብዛኞቹ የኢትዮጵያ ወረዳና ከተሞች ሕግ እና ሥርዓት ደግሞ፣ ያዩ እንደሚሉት ተናግቷል።
የፖለቲካ አቀንቃኝ እና ተንታኝ ገረሱ ቱፋ አንዱ ምክንያት ለዉጡ እታች አለመድረሱ ነዉ ይላሉ። የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ባለፈዉ ሐሙስ ባወጣዉ መግለጫ ግጭት እና ሁከት የሚቀሰቅሱትን «ሥልጣናቸዉን አላግባብ በመጠቀም የሕዝብ ሐብት ሲዘርፉ የነበሩ» ብሏቸዋል።የቀድሞ ባለሥልጣናት።  አቶ ገረሱም ከዋና ዋናዎቹ ምክንያቶች አንዱ መሆኑን ይቀበላሉ።
 ግጭት፤ ሁከት፣ ቀዉስ፣ ሥርዓተ አልበኝነቱ ለአብዛኛዉ ኢትዮጵያዊ አሳሳቢ፣ አስጊ መፍትሔዉም ግራ አጋቢ ይመስላል። አቶ ገረሱም ሥጋት-ፍርሐቱን ይጋራሉ። መፍትሔዉ ግን፣ የለዉጥ ኃይላት በጋራ እንዲቆሙ ከማድረግ በላይ፣ ብዙ አስጨናቂ አይደለም-እንደ አቶ ገረሱ።

Äthiopien Addis Abeba | Ring Road Stadion
ምስል DW/H. Melesse

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሰ