ዓረና የህወሓትን መግለጫ አወገዘ
ሰኞ፣ ሚያዝያ 7 2011
እሁድ ሚያዝያ 6፤ በመቐለ ኩሓ ተብሎ በሚታወቅ አካባቢ ወጣቶችና የፖለቲካ ፓርቲ አባላት በፖሊስ መደብደባቸውና መታሰራቸው ተቃዋሚው ዓረና ትግራይ ለሉአላዊነትና ዴሞክራሲ ገለፀ፡፡ እርምጃው የሕግ የበላይነት የጣሰ ብሎታል፡፡ በጉዳዩ ላይ የዓረናው ሊቀ መንበር አቶ አብርሃ ደስታ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ብቸኛው በትግራይ ክልል በተቃዋሚነት የሚንቀሳቀሰው ዓረና ትግራይ ለሉአላዊነትና ዲሞክራሲ በትላንትናው ዕለት እሁድ በመቐለ ኩሓ ወጣቶች በሰላማዊ እንቅስቃሴ ላይ በነበሩበት ወቅት የመንግስት የፀጥታ ሐይሎች ጥቃት እንደፈፀሙባቸው ገልፅዋል፡፡ በጥቃቱም የፓርቲው አባል፣ አክቲቪስቶችና ሌሎች ወጣቶች ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፣ ታስረዋል ብሏል፡፡ በፓርቲ የደረሰው ጥቃት ለማጣራት ቢንቀሳቀስም በፀጥታ ሐይሎች ክልከላ እንደደረሰባቸው ሊቀ መንበሩ አቶ አብረሃ ደስታ ዛሬ በፅሕፈት ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል፡፡ ዓረና እንዳለው ትላንት በፓሊስ ድብደባ ከተፈፀመባቸው የመቐለ ኩሓ ክፍለከተማ ነዋሪዎች መካከል የዓረና ማእከላይ ኮሚቴ አባልና የፓርቲው ቁጥጥር ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ፅጋቡ ቆባዕ እንደሚገኙበት ተነግሯል፡፡ ይህ ተግባር ሕጋዊነት የጎደለውና በዚህ ወቅት የማይጠበቅ ነው ያለው ፓርቲው ድርጊቱ የሚወገዝ መሆኑ አቶ አብረሃ ደስታ ገልፀዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ዙርያ ከመንግስት ወገን መረጃ ለማግኘት የመቐለ ኩሓ ክፍለ ከተማ ፖሊስና የፀጥታ ፅሕፈት ቤት ሐላፊዎች ለማግነት ሞክረን አልተሳካም፡፡ የመቐለ ከተማ ፀጥታና አስተዳደር ፅሕፈት ቤት ሐላፊ በበኩላቸው በጉዳዩ ዙርያ የደረሳቸው አንዳች መረጃ እንደሌለ ነግረውናል፡፡ በሌላ በኩል ዛሬ የዓረናው ሊቀ መንበር አቶ አብርሃ ደስታ በጋዜጣዊ መግለጫቸው በቅርቡ በህወሓት ማእከላይ ኮሚቴ በኩል ስለወጣው መግለጫ አስተያየታቸው ተጠይቀው ሲናገሩ "ህወሓት በመግለጫው ያቀረባቸው ውንጀላዎች ተቀባይነት የላቸውም" ብለዋል፡፡ የህወሓት ማእከላይ ኮሚቴ ዓርብ ዕለት አውጥቶት በነበረው የፅሑፍ መግለጫ በስም ያልጠቀሳቸው ሐይሎች ተልእኮ ተሰጥቷቸው በትግራይ ህዝብ ሰላምና ድህንነት ላይ አደጋ ለማድረስ እየሰሩ ነው በማለት ገልፆ እንደነበር ይታወሳል፡፡
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ