አወዛጋቢዋ ኢየሩሳሌም፤ የአንዲት ከተማ ታሪክ በሥዕል
ኢየሩሳሌም ከጥንት ከተሞች አንዷ ናት፤ በዚያም ላይ አወዛጋቢ። ለአይሁድ፣ ክርስቲያኖች እና ሙስሊሞች ኢየሩሳሌም ቅድስት ከተማ ናት። በዚህም ምክንያት እስከዛሬ በከተማዋ ጉዳይ ጭቅጭቅ አለ።
ኢየሩሳሌም፤ የዳዊት ከተማ
ብሉይ ኪዳን የሁለቱ ማለትም የይሁዳ እና እስራኤል ሥርወ መንግሥታት ንጉሥ ዳዊት ከክርስቶስ ልደት በፊት በ1000 ዓመተ ዓለም ኢየሩሳሌምንከኢያቡሳዉያንን አስለቅቆ እንደተቆጣጠረ ይናገራል። የመንግሥቱን መቀመጫ ወደ ኢየሩሳሌም በማዛወርም በዘመኑ የመናገሻዉ ዋና ከተማ እና የሃይማኖት ማዕከል አደረጋት። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለዉ የዳዊት ልጅ ሰሎሞን የመጀመሪያዉን ቤተ መቅደስ ለእስራኤል አምላክ ለየህዋ ሠራ። ኢየሩሳሌምም ለአይሁድ እምነት ማዕከል ሆነች።
የፋርስ ንጉሠ ነገሥት
የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር ሁለተኛ፤ ኢየሩሳሌምን ከክርስቶት መወለድ በፊት በ597 እና በድጋሚም በ586 ዓመተ ዓለም እንደወረራት መጽሐፍ ቅዱስ ይገልጻል። ንጉሥ ኢዮአቄምን እና የአይሁድን ከፍተኛ ባለስልጣናት ወደባሊሎን በግዞት በመዉሰድም ቤተመቅደሱን አፍርሷል። የፋርሱ ቂሮስ ባቢሎንን ሲወርር አይሁዳዉያን ከግዞት ወደኢየሩሳሌም ተመልሰዉ ቤተመቅደሳቸዉን ዳግም እንገነቡ ፈቅዶላቸዋል።
በሮም እና በቤዛንታይን ሥር
ከ63ዓ,ም ወዲህ ኢየሩሳሌም በሮማዉያን አገዛዝ ሥር ናት። በአይሁድ ኅብረተሰብ ዘንድ ተቃዉሞ ፈጥኖ በመነሳቱ በ66ዓ,ም የአይሁድ ጦርነት ተነሳ። ለአራት ዓመታት ቆይቶም በሮማዉያን ድል አድራጊነት ሲያበቃ የኢየሩሳሌም ቤተመቅደስ ዳግም ፈረሰ። ሮማዉያን እና ቤዛንታኖች ፍልስጤምን ለስድስት መቶ ዓመታት ያህል ገዝተዋል።
በአረቦች መወረር
ታላቋን ሶርያ ለመዉረር በሚያደርጉት ጉዞ ሙስሊም ጦረኞች ፍልስጤምም ደርሰዋል። ኸሊፋ ኦማር በሰጠዉ ትዕዛዝም በ637ዓ,ም ኢየሩሳሌም ተከብባ ተወርራለች። የሙስሊሞችን አገዛዝ በማጠናከሩ ወቅት የተለያዩ ተፎካካሪ ኃይሎች ፈራርሰዋል። ከተማዋ በተደጋጋሚ እየተከበበች ገዢዎቿ ብዙ ጊዜ ተፈራርቀዋል።
የመስቀል ጦርነት
ከጎርጎሪዮሳዊዉ 1070ዓ,ም ጀምሮ የገዛዉ የቱርክ ሙስሊም ኃይል ክርስቲያኑን ዓለም አስግቶ ነበር። በመጨረሻ ሊቀ ጳጳስ ዑርባን ሁለተኛ የመስቀል ጦርነት አወጁ። ባጠቃላይ ኢየሩሳሌምን ለመያዝ አዉሮጳዉያን በ200 ዓመታት ዉስጥ አምስት ጊዜ የመስቀል ጦርነት አካሂደዋል። በመካከሉም ያ ተሳክቶላቸዋል። ነገር ግን በ1244ዓ,ም የመስቀል ጦረኞቹ ከተማዋ ላይ የነበራቸዉን ኃይል አጡ እና በድጋሚ ከተማዋ በሙስሊሞች አገዛዝ ሥር ወደቀች።
ኦቶማኖች እና ብሪታኒያዉያን
በጎርጎሮዮሳዊዉ 1535 ግብፅ እና አረቦች በኦቶማን ከተወወሩ በኋላ ኢየሩሳሌም የኦቶማን መንግሥት አስተዳደር መቀመጫ ክፍለ ግዛት ሆነች። የመጀመሪያዎቹ አስርት ዓመታት የቱርክ አገዛዝ በከተማዋ ትርጉም ያለዉ መሻሻያ አምጥቷል። በ1917 ብሪታንያዎች በቱርክ ወታደሮች ላይ ድል ሲያገኙ ፍልስጤም በብሪታንያ አገዛዝ ሥር ገባች። ኢየሩሳሌምም ያለምንም ዉጊያ ወደብሪታንያ እጅ ገባች።
የተከፋፈለች ከተማ
ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት በኋላ ብሪታኒያ ፍልስጤም ላይ የነበራት ስልጣን አከተመ። የተመድ ከሆሎኮስት ለተረፉት አይሁዳዉያን መኖሪያ ሀገሪቱን ለመክፈል ተሰበሰበ። አንዳንድ የአረብ ሃገራት ከእስራኤል ላይ ጦርነት አካሂደዉ ከፊሉን የእስራኤልን ግዛት ወረሩ። እስከ ጎርጎሪዮሳዊዉ 1967 ምዕራቡ ለእስራኤል፤ ምሥራቁ ደግሞ ለዮርዳኖስ ሆኖ ተከፈለ።
ምሥራቅ ኢየሩሳሌም ዳግም ወደእስራል ተመልሳለች
በጎርጎሪዮሳዊዉ 1967 እስራኤል ከግብፅ፣ ከዮርዳኖስ እና ከሶርያ ጋር የስድስት ቀን ጦርነት አካሂዳለች። ሲናን፣ የጋዛ ጎዳናን፣ ምዕራብ ዮርዳኖስን፣ የጎላን ኮረብታዎች እና ምሥራቅ ኢየሩሳሌምን ያዘች። የእስራኤል ወታደሮችም ከ1949ዓ,ም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አሮጌዉ ከተማ እና ወደ መጮኺያዉ ግንብ ተመልሰዉ መግባት ቻሉ። ምሥራቅ ኢየሩሳሌም በይፋ የተገነጠለች ሳትሆን በአስተዳደር ተጣምራለች።
ሙስሊሞች ወደእስራኤል ሃይማኖታዊ ጉዞ ማድረግ ይችላሉ
እስራኤል በእስልምና እጅግ ተፈላጊ ከሚባሉት ሦስተኛዉ ስፋራ እዚህ ይገኛል፤ ሙስሊሞች ወደተቀደሰዉ ስፍራዉ እንዳይገቡ አትከለክልም። የቤተ መቅደሱ የሚገኝበት ተራራ በሙስሊም አስተዳደር ሥር የሚተዳደር ነዉ፤ ሙስሊሞች ወደዚያ በመግባት ከአላቅሳ መስጊድ አቅራቢያ በሚገኘዉ ወርቃማ ጣሪያ ባለዉ መስጊድም መጸለይ ይችላሉ።
የመጨረሻ ይዞታዋ ዛሬም ግልጽ አይደለም
ኢየሩሳሌም ዛሬም በእስራኤል እና ፍልስጤም መካከል ሰላም ለማምጣት እንቅፋት እንደሆነች ነዉ። በጎርጎሪዮሳዊዉ 1980 እስራኤል መላ ከተማዋን «ዘለዓለማዊ እና የማትከፈል ዋና ከተማ» ስትል አዉጃለች። በ1988 ዮርዳኖስ የምዕራብ የዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ እና ምሥራቅ ኢየሩሳሌምን የፍልስጡጤም ግዛት ናቸዉ ብላ በይፋ አዉጃለች። እናም የከተማዋ ምሥራቃዊ ክፍልንም በነባቤ ቃል የፍልስጤም ዋና ከተማ ብላዋለች። ሸዋዬ ለገሠ/ ነጋሽ መሐመድ