1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ዳግም መጀመር ለመቐለ ነዋሪዎች የሰጠው ተስፋ

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 1 2015

የትግራይ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ዳግም ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የሐይል ቋት ተገናኝቶ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ሥራቸው በኃይል እጦት የተደናቀፈባቸው ነዋሪዎች ችግሮቻቸው እንደሚቀረፉ ተስፋ ያደርጋሉ። በሣምንቱ መጀመሪያ መቐለን ጨምሮ የክልሉ ከተሞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት አግኝተው ሰዎች ተቋርጦ ወደነበረ ሥራቸው እየተመለሱ ነው።

https://p.dw.com/p/4Klm3
Äthiopien Mekelle | Provinzhauptstadt | Region Tigray
ምስል Million Haileselassie/DW

በትግራይ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ዳግም መጀመር ለመቐለ ነዋሪዎች የሰጠው ተስፋ

መቐለ ጨምሮ የተለያዩ የትግራይ ከተሞች ከ18 ወራት በኋላ የኤሌክትሪክ ሐይል ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የሐይል ቋት ማግኘት መጀመራቸው በክልሉ ተስተጓጉሎ የቆየ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንደሚያነቃቃ ተገለፀ። በመቐለ ያነጋገርናቸው በተለያየ የስራ መስክ የተሰማሩ ዜጎች የተጀመረው የኤሌክትሪክ ሐይል አገልግሎት በማድነቅ፥ እስካሁን ያልተከፈቱ እንደ ስልክ፣ ባንክ፣ ኢንተርኔት የመሳሰሉ አገልግሎቶች ዳግም እንዲመለሱ ይጠይቃሉ።

በመቐለ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሐይል ሰሜን ሪጅን ሰራተኞች እንዳረጋገጡልን ከሕዳር 27 ቀን 2015 ማምሻው ጀምሮ የትግራይ ርእሰ ከተማ መቐለ ጨምሮ መኮኒ፣ ውቅሮ፣ ዓዲግራት፣ ዓብይዓዲ እና ሌሎች በአካባቢው ያሉ ከተሞች ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የሀይል ቋት የኤሌክትሪክ ሐይል ማግኘት ጀምረዋል። 

ትግራይ ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የሐይል ቋት ታገኘው የነበረ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ከሰኔ ወር 2013 ወዲህ ተቋርጦ ነበር። በዚህ መካከል እየተቆራረጠ እና በውስን መጠን በትግራይ ከሚገኝ የሐይል ምንጭ፣ በክልሉ አስተዳደር አስተባባሪነት የኤሌክትሪክ ሐይል ለህዝቡ ይቀርብ ነበር።

ከሕዳር 27 ቀን  ከ11 ሰዓት ጀምሮ ከ18 ወራት በኋላ የኤሌክትሪክ ሐይል አገልግሎት ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ሐይል ቋት ለመቐለ ጀምሮ ለተለያዩ የትግራይ ከተሞች መቅረብ መጀመሩ የነበረው የሐይል እጦት ያቃልላል ተብሎ ይገመታል።

ሚሊዮን ኃይለስላሴ
እሸቴ በቀለ