1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያውያን ማህበር በኑርንበርግ 

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 8 2010

ወደ ሥራው ከመግባታቸው በፊት በጀርመን ህግ መሠረት አስፈላጊ የሆነውን ሥልጠና መውሰዳቸውን የድርጅቱ ምክትል ሊቀ መንበር አቶ አህመድ ሲራጅ ይናገራሉ። አቶ አህመድ እንዳሉት ይህን ስልጠና መውሰዳቸው በአካባቢያቸው በሚገኝ ትልቁ የስደተኞች ካምፕ ውስጥ በኤድስ ላይ ያተኮረ የምክር አገልግሎት መስጠት አስችሏቸዋል። 

https://p.dw.com/p/33ATC
Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.

ስደተኞችን የሚረዳ የኢትዮጵያውያን ማህበር

መጠሪያው «የህብረት ክንድ በኤድስ ላይ» ይባላል። በደቡባዊ ጀርመንዋ ከተማ በኑርንበርግ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የዛሬ 15 ዓመት ያቋቋሙት ማህበር ነው። 15 ሆነው ነበር የመሰረቱት። በኢትዮጵያ በኤድስ ወላጆቻቸውን ያጡ ህጻናትን የመርዳት ዓላማ ይዞ ነበር የተመሰረተው። ለማህበሩ ምሥረታ መነሻ  የሆናቸውም ከሀገር ቤት ይቀርብላቸው የነበሩ የእርዳታ ጥሪዎች እና የማህበሩ መስራቾች ኢትዮጵያ ሄደው ያዩት የችግሩ ስፋት እንደነበረ ያነጋገርኳቸው የማህበሩ መሥራቾች እና እስካሁንም ሥራውን በማከናወን ላይ የሚገኙት 3 የማህበሩ አመራሮች ተናግረዋል። ወደ ሥራው ከመግባታቸው በፊትም በጀርመን ህግ መሠረት አስፈላጊ የሆነውን ሥልጠና መውሰዳቸውን የድርጅቱ ምክትል ሊቀ መንበር አቶ አህመድ ሲራጅ ይናገራሉ። አቶ አህመድ እንዳሉት ይህን ስልጠና መውሰዳቸው በአካባቢያቸው በሚገኝ ትልቁ የስደተኞች ካምፕ ውስጥ ስለ ኤድስ የምክር አገልግሎት መስጠት አስችሏቸዋል። 

አቶ አህመድ ትልቁ የስደተኞች ካምፕ የሚሉት ኢትዮጵያውያን ስደተኞችም የነበሩበትን በባየርን ፌደራዊ ክፍለ ሃገር የሚገኘውን የሲሪንዶርፍ የስደተኞች መጠለያ ነው። እነ አቶ አህመድ ከኑርንበርግ 20 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው በዚህ መጠለያ ካዩዋቸው ችግሮች በመነሳት ለስደተኞች ተጨማሪ አገልግሎት መስጠት ቀጠሉ ።ወይዘሮ ገነት የማነ የማህበሩ መሥራች እና የገንዘብ ያዥ ናቸው።

 ጎርጎሮሳዊው 2014 በርካታ ስደተኞች ወደ ጀርመን መግባት የጀመሩበት ወቅት ነበር። እናም አቶ አህመድ እንዳስረዱት ያኔ ፈታኝ ወቅት ነበር ለማህበራቸው እና አባላቱ። ከዚያ በኋላ ለስደተኞች የሚሰጡት አገልግሎት በመጠንም በዓይነትም እየሰፋ ሄደ  

አቶ ዮናስ ብዙነህ የማህበሩ ሊቀመንበር ናቸው። ጀርመን ከመጡ 24 ዓመት ሆኗቸዋል። ከዛሬ 15 ዓመት አንስቶ በዚህ ማህበር ውስጥ በንቃት ይሳተፋሉ። ከሁለት ሳምንት በፊት በአውሮጳ እና ጀርመን ፕሮግራም ችግራቸውን የተናገሩ ደቡብ ጀርመን ጥገኝነት የጠየቁ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ብዙ ዓመት ጀርመን የቆዩ ኢትዮጵያውያን በአካባቢያቸው ቢኖሩም እንደማይረዷቸው ተናግረው ነበር። አቶ ዮናስ ማህበራቸው እና አባላቱ ግን ስደተኞችን ለመርዳት የበኩላቸውን ከማድረግ ወደ ኋላ እንዳላሉ ያስረዳሉ።
   
 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በጎርጎሮሳዊው አቆጣጠር በ2017 ሲርንዶርፍ ከተባለው የስደተኞች መጠለያ፣ከኑርንበርግ 100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደ ሚገኘው የሬግንስቡርግ ካምፕ ቢወሰዱም እነ አቶ አህመድ ርቀት ሳይገድባቸው ስደተኞችን መርዳት መቀጠላቸውን ገልጸዋል። «የህብረት ክንድ በኤድስ ላይ»በተባለው ማህበር ሦስቱ መሥራቾች በንቃት ሲሳተፉ ሌሎች አባላት ደግሞ የተለያዩ እገዛዎች ያደርጉላቸዋል። ይሁን እና በዚህን መሰሉ የግብረ ሰናይ ሥራ ውስጥ የመሳተፍ ፍላጎት የሌላቸውም ኢትዮጵያውያንም አሉ። ምክንያታቸውን አናውቅም ይላሉ ወይዘሮ ገነት
«የህብረት ክንድ በኤድስ ላይ»የተባለው ኑርንበርግ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ማህበር አቶ ዮናስ እንደሚሉት ወደፊት ለስደተኞች እገዛ የሚያደርጉ ሌሎች አገልግሎቶች ላይ አትኩሮ የመስራት እቅድ አለው።

Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.
Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.

ኂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ