ሱዳኖች በጋራ ለመስራት ተስማሙ
ሰኞ፣ ሐምሌ 1 2011
ሱዳኖች የ30 ዘመን ገዢያቸዉን ባስወገዱ ማስግሥት ወታደር-ሲቢል በሚል እሁለት ተከፍለዉ እንደባላንጣ ሲወጋገዙ፤ሲሻኮቱ፤ ብዙ አምርረዉ እንደ ጠላት ሲገዳደሉ ወራት አስቆጠሩ።በስተጨረሻዉ ግን ሽማግሌዎችን ተቀብለዉ እንደ ኩርፈኛ ተደራድረዉ እንደ አንድ ሐገር ዜጋ የጋራ ሐገራቸዉን በጋራ ለመምራት ተስማሙ።አርብ።የሱዳኖች ስሜት በዲፕሎማቱ አንደበት፣፦
በሱዳን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ልዩ መልዕክተኛና አደራዳሪ አምባሳደር ማሕሙድ ድሪር።አምባሳደር ማሕሙድ የድርድሩን ሒደት፣ ፈተና፣ የዉጤቱን ተስፋ ያስረዱናል አብራችሁን ቆዩ።ለአምባሳደር ማሕሙድ ድሪር ባለፈዉ ሳምንት ስደዉልላቸዉ «ምጥ የሚያጣድፋት እናትን ለመርዳት እንደሚራወጥ አዋላጅ እየተጣደፍን ነዉ» ብለዉኝ ነበር።በሳምንቱ ዛሬ።
ለሽፈት ወይም ላለመሳካት ባለቤት ማግኘት ይከብዳል ይባላል፤ ለድል ወይም ለጥሩ ዉጤት ግን ባለቤት ለመሆን የማይረወጥ የለም።የሱዳኖች መስማማት እንደተሰማም ካደራዳሪዎች ዝርዝር የብዙ መንግስታት ስም ገብቷል።
ሱዳን።ከአፍሪቃ ሶስተኛዋ ሰፊ ሐገር ናት።የ41 ሚሊዮን ሕዝብ ሐገር።ከግብፅ እስከ ደቡብ ሱዳን፣ ከቀይ ባሕር እስከ ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ 6 ሐገራትን እና ቀይ ባሕርን የምታዋስን ስልታዊ፣ በአፍሪቃ ፖለቲካ ዐብይ ሚና የምትጫወት ታሪካዊ፣ ጠቃሚም ሐገር ናት።የሱዳን ሪፐብሊክን የሚያብጥ ቀዉስ ዳፋዉ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለብዙ ጎረቤቶችዋ የሚተርፍ ነዉ።
አምባሳደር ማሕሙድ «ጎረቤት ሐገር እየተቃጠለ እኛ በሰላም አንኖርም» ዕይነት ይላሉ።
ስምምነቱ።
ላዕላይ ምክር ቤቱን ከወታደራዊዉ የሽግግር ምክር ቤት የሚወከሉ የጦር ጄኔራል ለመጀመሪያዉ 21 ወራት፣ ከነፃነትና የለዉጥ ኃይላት የሚወከሉ ፖለቲከኛ ደግሞ ለ18 ወራት ይመሩታል።ካቢኔዉ ከመከላከያና ከሐገር ዉስጥ ሚንስትሮች በስተቀር የተቀሩት አባላቱ ከሲቢሎች የሚሾሙ ናቸዉ።
«የተወካዮች» የተባለዉ ምክር ቤት ከሚያስተናብራቸዉ አባላት 67 ከመቶዉ ሲቢል፣ 33 ከመቶዉ ወታደሮች ይሆናሉ የሚለዉ ሐሳብ እስካሁን የሚያግባባ ይመስላል።በተቃዉሞ ሰልፉ ወቅት የተገደሉ ሰልፈኞችን አሟሟት የሚያጣራ ገለልተኛ ኮሚሽን ለመመስረትም ተስማምተዋል።
ስምነቱን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣የአፍሪቃ ሕብረት፣የአዉሮጳ ሕብረት፣ ዩናይትድ ስቴትስና ከሱዳን ተቀናቃኝ ኃይላት አንዱን ወይም ሌላዉን ይደግፋሉ የሚባሉት የአረብ ሐገራትም ደግፈዉታል።ሁለት የሱዳን የፖለቲካ ፓርቲዎችን ግን አለመቀባላቸዉ ተዘግቧል።አምባሳደር ማሕሙድ ድሪሪን እናመሰግናለን።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሰ