1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጠገዴ ወረዳ በመከላከያ ቁጥጥር ስር ነዉ ተባለ

ሐሙስ፣ ጥቅምት 26 2013

ረቡዕ ውጊያ ሲካሄድበት የነበረው የአማራ ክልል ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጠገዴ ወረዳ ቅራቅር አካባቢ ዛሬ ሰላማዊ ሆኖ መዋሉን ነዋሪዎቹ ተናገሩ፣ በሌላ በኩል በዚሁ ዞን ምድረ ገነት ወይም አብደራፊ በተባለ አካባቢ ሌል ግጭት መፈጠሩን የአካባቢው ነዋሪ አመለከቱ፡፡

https://p.dw.com/p/3kvXD
Äthiopien - Gonder
ምስል DW/A. Mekonnen

ሰራዊቱ የትግራይ ፀገዴ ዋና ከተማ ንጉስን ተቆጣጥሮአል

ረቡዕ ውጊያ ሲካሄድበት የነበረው የአማራ ክልል ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጠገዴ ወረዳ ቅራቅር አካባቢ ዛሬ ሰላማዊ ሆኖ መዋሉን ነዋሪዎቹ ተናገሩ፣ በሌላ በኩል በዚሁ ዞን ምድረ ገነት ወይም አብደራፊ በተባለ አካባቢ ሌል ግጭት መፈጠሩን የአካባቢው ነዋሪ አመለከቱ፡፡ በትግራይ ልዩ ኃይልና በፌደራሉ መንግስት የፀጥታ ኃይል መካከል ትናንት የተፈጠረው ግጭት በአንዳንድ ቦታ ጋብ ሲል በሌላ በኩል ደግሞ አዲስ ግጭቶች መፈጠራቸውን የየአካባቢው ነዋሪዎች ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡  ትናንት ረቡዕ ግጭት ከነበረባቸው አካባቢዎች አንዱ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጠገዴ ወረዳ ቅራቅር አካባቢ ሲሆን አካባቢውን የመከላከያ ሰራዊት በመቆጣጠሩ ግጭቱ መቆሙን የአካባቢው ነዋሪ አመልክተዋል። ሰራዊቱ ወደ ትግራይ ፀገዴ በመግባትም የወረዳውን ዋና ማዕክል ከተማ ንጉስን መቆጣጠሩንም እኝሁ ነዋሪ ገልፀዋል።  ግጭቱ ከመፈጠሩ በፊት ከበፊቱ የተለየ ነገር እንዳልነበር የሚናገሩት አስተያየት ሰጪዎቹ ክስተቱ ድንገተኛ እንደነበር አስረድተዋል፡፡ አንዳንድ ተቋማትን ከመጠበቅ የተለየ ነገር አልነበረም ብለዋል፡፡ አስተያየት ከሰጡን አንደኛው እንዳሉት በፀጥታ ችግር ምክንያት መንገድ ዝግ ስለነበር ለአንድ አመት ያህል 2 ሰዓታ የሚወስደውን የቅራቅር ጎንደር መንገድ በሌላ መንገድ ዞን ስለምንሄድ ረጅም ጊዜ ይስድብን ነበር ሲሉ አስረድተዋል። ሌላው የዚሁ አካባቢ ነዋሪ እንዳሉት አሁን አካባቢው ሰላም በመሆኑ የአካባቢው ሚሊሽያ ከሚተኩሰው የደስታ ጥይት በስተቀር ምንም ነገር እንደሌለ ተናግረዋል። ዛሬ አነጋጉ ላይ በአማራ ክልል አብደራፊ ምድረ ገነት አካባቢ ግጭት እንደነበር ደግሞ አንድ አስተያየት ሰጪ አመልክተዋል፣ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ከቀኑ 10 ድረስ የተኩስ ድምፅ እየተሰማ ቢሆንም እየራቀ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡  አንድንድ አስተያየት ሰጪዎች ችግሩ እየሰፋ ሄዶ ከፍተኛ ሰብአዊ ጉዳት ከመድረሱ በፊት አሁንም ሁለቱ አካላት ለድርድር ዝግጁ እንዲሆኑ ጠይቀዋል።  የግንኙነት መስመሮች ሁሉ ዝግ በመሆናቸው ከትግራይ ክልል በኩል ያለውን ሁኔታ አስተያየት ማካተት አልተቻለም።

ዓለምነዉ መኮንን 

አዜብ ታደሰ 

እሸቴ በቀለ