1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«መንግሥት እና ሕዝቡ ጣናን ለመታደግ ትኩረት ይስጡ

ዓርብ፣ ሰኔ 5 2012

የጣና ሐይቅ ህልውና አደጋ ላይ መውደቅ የውሀው መጥፋት ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ እንደሚያስከትል በሐይቁ እየዋኙ ያደጉ የባሕር ዳርና አካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ ጣና ውሀ ብቻ አይደለም ሲሉም በቁጭት ይናገራሉ፡፡

https://p.dw.com/p/3dgQ6
Invasive Species, Everyday Africa
ምስል Maheder Haileselassie

«ጣና ታሟል»

"የጣና ልጆች ጩኸት!"

የጣና ሐይቅ ህልውና አደጋ ላይ መውደቅ የውሀው መጥፋት ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ እንደሚያስከትል በሐይቁ እየዋኙ ያደጉ የባሕር ዳርና አካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ ጣና ውሀ ብቻ አይደለም ሲሉም በቁጭት ይናገራሉ፡፡የጣና ሐይቅ ካለፉት 8 ዓመታት ወዲህ ህልውናውን የሚፈታተኑ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ  ፈተናዎች እንደገጠሙት በባሕር ዳር ከተማ የሚኖሩና ከሐይቁ ጋር ቁርኝት ያላቸው ነዋሪዎች አመልክተዋል፡፡በተለይ እምቦጭ የተባለው አረም ሐይቁን በፍተኛ ሁኔታ እንደወረረውና እስካሁን የተደረጉ ጥረቶች ሁሉ ውጤት እንዳላመጡ ተናግረዋል፡፡ ወደ ሐይቁ የሚለቀቁ ፍሳሶችና ፕላስቲክ የመሳሰሉ ቁሳቁሶች ሌሎች ለሐይቁ ህልውና ጥያቄ ውስጥ መውደቅ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡የባህር ዳር ነዋሪውና ክልጅነታቸው ጀምሮ በሐይቁ እየዋኙ፣ እየጠጡ ያደጉት አቶ መስፍን አድማሱ ጣና የገጠመውን ፈተና በተመለከተ ለዶይቼ ቬለ አብራርተዋል፡፡ሌላዋ የባሕርዳር ከተማ ነዋሪ ወ/ሮ ብዙነሽ ይሁኔ እንደሚሉት ደግሞ በጣና ያልተዝናና፣ ዓሳዎቹን ያልተመገበ፣ በውስጡ ባሉ ሐይማኖታዊና መንፈሳዊ በረከቶች ያልተባረከ የባሕር ዳርና ለአካባቢው ነዋሪ ማግኘት አይቻልም ይላሉ፡፡አሁን በሐይቁ ላይ የተደቀነው ተፅዕኖ ግን ከፍተኛና ልንመልሰው የማንችለው አደጋ እያመጣ አንደሆነ ነዋሪዎቹ ይናገራሉ፡፡ሌላው በጣና ገዳማትና አድባራት ዙሪያ ቅርበት ያላቸው አቶ ቴዎድሮስ ካሳሁን የጣና ህመምም አፋጣኝ መፍትሄ ካልተገኘለት፣ ለከተማዋ ህልውና አደጋ ይፈጥራል፣ በጣና ሐይቅ ላይ ህይወታቸውን የመሰረቱ ሰዎች ለአደጋ ይጋለጣሉ፣ የመዝናኛው ዘርፍም ይዳካማል ብለዋል፤በተለይ ከ30 በላይ የሚሆኑ ጥንታዊ አድባራትና ገዳማት፣ እንዲሁም ዘመን ጠገብ የሆኑ ቅርሶች፣ የነገስታት አፅምና በርካታ ሐይማኖታዊና ባህላዊ ሀብቶች በጣና ሐይቅ ገዳማት እንደሚኖሩ ጠቅሰው ጣና አደጋ ከደረሰበት እነኝህ ሁሉ እንደማይኑሩ ነው ስጋታቸውን የተናገሩት፡፡ጣና ሐይቅ የዓለማያን እድል ካጋጠመው አጠቃላይ የብዝሐ ሕይወት መናጋት እንደሚፈጠርም ነው አስተያየት ሰጪዎቹ  በቁጭት ያስረዱት፡፡የአማራ ክልል የአካባቢ የደንና የዱር እንስሳት፣ ጥበቃና ልማት ባለስልጣና ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር በላይነህ አየለ ጣናን ከተጋረጠበት አደጋ ለመታደግ የህዝብ ንቅናቄ በመፍጠር ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዋል፡፡የባህርዳር ነዋሪው አቶ ቴዎድርስ ካሳሁን ግን የጣናን ችግር በዘመቻ አጠፋለሁ ብሎ ማስብ ትክክል እንዳልሆነ ነው የሚናገሩት፤ ይልቁንም በጊዜ የተገደበ ጠንካራ ፕሮጀክት ቀርፆ መስራቱ የተሸለ መንገድ እንደሚሆን አመልክተዋል፡፡በአጠቃላይ መንግስትና ህዝብ ለሐይቁ ትኩረት እንዲሰጥና የጣና ሐይቅን ከመጥፋት እንዲታደጉት ነዋሪዎቹ ጠይቀዋል፡፡

Wasserhyazinthen  Lake Tana Äthiopien
ምስል Adugnaw Admas
Äthiopien Kampagne Save Lake Tana
ምስል Kalkidan Tsena

አለምነው መኮንን

ታምራት ዲንሳ

አዜብ ታደሠ