1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፕሬዝደንታዊ ምርጫ በቤኒን

ሰኞ፣ የካቲት 27 1998

ምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር ቤኒን በትናንትናዉ ዕለት ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ አካሄደች።

https://p.dw.com/p/E0iz

የአሁኑንና የቀድሞ የአገሪቱን ፕሬዝዳንቶች ያላሳተፈዉ ይህ ምርጫ 26 ፕሬዝዳንታዊ እጩዎችን ያካተተ ነዉ። ከዚህ በመነሳትም ታዛቢዎች እንደሚሉት የትኛዉም ተወዳደሪ በመጀመሪያዉ ዙር የምርጫ ሂደት በሰፊ ብልጫ ያሸንፋል የሚባልበት አይደለም። ሆኖም ከፍተኛ የመራጭ ህዝብ ተሳትፎ የታየበት ይህ የቤኒኑ ምርጫ ከትችት የፀዳ አይደለም ተብሏል። በስልጣን ላይ የሚገኙት ፕሬዝደንት ግን የወሰደዉን ያህል ጊዜ ወስዶ የተጣራ ዉጤት ይፋ ይሆናል የሚል አቋም አላቸዉ።

የቤኒን የምርጫ ጣቢያዎች ዛሬ ንጋት ላይ በአገሩ አቆጣጠር ነበር ተግባራቸዉን አጠናቀዉ ለመዘጋት የበቁት ለምርጫ ከወጣዉ ህዝብ ብዛት የተነሳ።
ስልጣን ለመልቀቅ የተዘጋጁት የአሁኑ የቤኒን ፕሬዝደንት ማቲዉ ኬሬኩ ተተኪያቸዉን ለመምረጥ የተካሄደዉ ምርጫ ማጭበርበር እንዳይታከልበት አስጠንቅቀዋል።
የምርጫ ኮሚሽኑ ፕሬዝደንት ሲልቪያን ኖዋቲን ዛሬ ማለዳ እንደተናገሩት በምርጫ ጣቢያዎቹ የነበረዉ ሂደት አብቅቷል።
ቆጠራዉን በማዕከላዊ ደረጃ በማካሄድ ላይ መሆናቸዉንም ጨምረዉ በመግለፅ ዉጤቱን በተባለዉ ቀን ግልፅነት በተላበሰ መልኩ እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል።
የቀድሞዉ አንባገነናዊ ማርክሲስት ኋላም በምርጫ ፕሬዝደንት የሆኑት ኬሬኩ ላለፉት 30 ዓመታት ቤኒንን ገዝተዋል።
እናም በምርጫዉ ላይ ሃሳባቸዉን ሲገልፁ ከዚህ ለዘለቁ ዘመናት በስልጣን ለመስንበት ማጭበርበር ቢፈልጉ ኖሮ የመጀመሪያዉ የድምፅ ዉጤት ከመታወቁ ከወራት በፊት ይሞክሩት ነበር።
ለጡረታ የተዘጋጁት የ72 ዓመቱ ኬሬኩ በአዲሱ የቤኒን ዲሞክራሲያዊ ህገ መንግስት መሰረት ለምርጫ ለመወዳደር በጣም አርጅተዋል።
ህገ መንግስቱን ባለመቀየር በወሰዱት የጡረታ መዉጣት እርምጃም 4ሚሊዮን የሆን መራጭ ህዝብ ከ26 እጩዎች መካከል በእግራቸዉ የሚተካዉን ለመምረጥ ወጥቷል።
ለዘጋቢዎች እንደገለፁትም ግልፅና ነፃ ይሆናል ብለዉ ተስፋ ያደረጉበት ምርጫ እንደታሰበዉ ይሆናል የሚል እምነት ያሳደሩ አይመስሉም።
በእሳቸዉ እምነትም ተወዳዳሪዎቹ ሁሉ ይህን ያዉቃሉ ግን ምንም እስካሁን አልተናገሩም፤ የምርጫዉን ሂደት የሚያከናዉነዉ አካልም እንዲሁ ስለግልፅነትና ነፃ ምርጫነቱ ያለዉ የለም።
የበኩላቸዉን የምርጫ ድምፅ ኮቶኑ ከተማ ከሰጡ በኋላ እንደተናገሩት ቤኒን በተጭበረበረ ሁኔታ ምርጫ አካሄደች እንዲባል አይፈልጉም።
ያንንም ለማረጋገጥ ሲሉ የምርጫዉ ዉጤት ሶስትም ሆነ አራት ወራት ቢወስድም ተጣርቶና ተረጋግጦ እንዲወጣ ነዉ የሚፈልጉት በእሳቸዉ አባባል ልክ እንደዩናይትድ ስቴትስ።
ኖዋታን በበኩላቸዉ በአገሪቱ ዙሪያ ህዝቡ ለምርጫ በነቂስ መዉጣቱን ሲገልፁ በፓርቶ ኖቮ ከተማ በበርካታ የምርጫ ጣቢያዎች የተዘዋወሩት የአጃንስ ፍራንስ ፕረስ ዘጋቢዎች ለምርጫ የወጣዉን ህዝብ በ70 ከመቶ ገምተዉታል።
የቤኒን ህዝብ ለዉጥ ፈልጓል ሙስና አምባገነንነትና በስልጣን አላግባብ መጠቀም ይብቃ በሚል። ከምርጫዉ በፊት ህዝቡ ምን ተስፋ እንደሚያደርግ ተጠይቆ ነበር። በምርጫዉ ተሳታፊ የሆኑ አንዲት ዜጋ እንዲህ ይላሉ
«ቤኒን ኋላቀር አገር ናት፤ ስለሆኑም ልማት ለዚች አገር አስፈላጊዋ ነዉ። ቤኒን ብዙ የተለያየ ችግር ያለባት አገር ስለሆነች የፖለቲካና የህግ ሰዉ ብሎም የአገሪቱን ፍላጎት መከላከል የሚችል ፕሬዝዳንት ነዉ የሚያስፈልጋት። የበፊቱ ኬሬኩ የራሱ ዓላማ ነበረዉ።»
ምንም እንኳን ፕሬዝደንቱ እንደሌሎች መሰል የአፍሪካ መሪዎች ህገ መንግስት አሻሽለዉ በስልጣን ለመሰንበት አለመጣራቸዉ ገንቢና አንድ እርምጃ ቢባልላቸዉም ስርዓታቸዉ በወጣት የአገሪቱ ዜጎች እንዲህ ነዉ የሚታየዉ፤
«በቤኒንን ህዝብ ደስታ የሚቀንሰዉ በአገሪቱ ያለዉ ሙስናና አምባገነንነት ማብቃት አለበት። በመሆኑም እኔ የምፈልገዉ አዲሱ ፕሬዝደንት ጥሩ እንደሌሎቹ ሚኒስትሮችና የመንግስት ሠራተኞች ብልሹ ያልሆነ እንዲሆን ነዉ።»
ይህን ሀሳብ ሌሎችም ይጋሩታል ለምሳሌ ከቤኒን የሶሻሊስት ፓርቲ ማዉሪስ ፋንግኖን በአገሪቱ የታየዉን ሙስና በተመለከተ እንዲህ ይላሉ
«ቤኒን ዉስጥ ዴሞክራሲያዊ አርአያነት ይታያል ይባላል ያ መቶ በመቶ ትክክል ነዉ። በዚሁ ስርዓት ዉስጥ ግን ብዙ ገንዘብ ጠፍቷል። አጥፊዎቹም በነፃ ይዘዋወራሉ ጭራሹንም ይሾማሉ። ይህ ዲሞክራሲ አይደለም። የቤኒ ህዝብም የሚፈልገዉ ይህን አይደለም።»
ይህን መሰሉ የህዝብ የለዉጥ ፍላጎት በተንፀባረቀበት የቤኒን የምርጫ ክንዉን የምርጫ ቅስቀሳ አስተባባሪዎች እንደሚሉት የምርጫ ቁስቁስ መጥፋት፤ ዘግይቶ የምርጫ ጣቢያዎችን የመክፈት ከተመዘገበዉ የመራጭ ድምፅ በላይ በምርጫዉ ተመዝግቦ መገኘትና የተዛቡ አሰራሮች ታይተዋል።
ለዚህ ዓለም ዓቀፉን ህብረተሰብና የምርጫ ታዛቢዎችን ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጡት እንጠይቃለን ብለዋል።
ቤኒን በመድበለ ፓርቲ ስርዓት ከገባች ከ1982ዓ.ም. ወዲህ ትናንት የተካሄደዉ ምርጫ ለአራተኛ ጊዜ መሆኑ ነዉ።