ፓሪስ፤ በፈረንሳይ ምርጫ የማክሮ ድልና አስተያየት
ሰኞ፣ ሚያዝያ 30 2009
የአዉሮጳ ኅብረት ኮሚሽን ፕሬዝደንት ዦን ክላዉድ ዩንከር እሳቸዉ የሚታገሉለት ለዜጎቹ የቆመ «ጠንካራ እና ዉጤታማ አዉሮጳ» የሚለዉ ሃሳብ የፕሬዝደንትነቱን መንበር በመያዙ የተሰማቸዉን ደስታ ለማክሮን ገልጸዋል። በተመሳሳይ የቀኝ ክንፍ ፖለቲከኞችን ጨምሮ ተቃዋሚዎቻቸዉን አሸንፈዉ የኔዘርላንድስ ጠቅላይ ሚኒስትርነታቸዉን ባለፈዉ መጋቢት ያረጋገጡት ማርክ ሩተ ለማክሮ የደስታ መግለጫ ልከዋል። ድላቸዉን እንዳረጋገጡ ከጀርመኗ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጋር በስልክ የተነጋገሩት ማክሮ በቅርቡ በርሊንን እንደሚጎበኙ፤ በብሬግዚት ጉዳይ ላይም ከብሪታንያዋ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ ጋር እንደሚነጋገሩ አስታዉቀዋል። የ39ዓመቱ ቀጣዩ የፈረንሳይ ፕሬዝደንት ኢማኑዌል ማክሮ በሀገራቸዉም አዲስ ምዕራፍ ለመክፈት መዘጋጀታቸዉን ተናግረዋል።
«የዴሞክራሲያችንን አስፈላጊነት መከላከል በሕዝቡ ሕይወት ዉስጥ ዳግም ስነምግባርን የመጨመር ጉዳይ ነዉ። ኤኮኖሚያችንን ማጠናከር እና ማሻሻል እንዲሁም አዲስ አይነት ራስን የመከላከል ስልት መገንባትንም ያካትታል። በትምህርት፣ በሥራም ሆነ በባህል ዉስጥ ለሁሉም የሚሆን ቦታ ማመቻቸትም ያስፈልጋል።»
የፊታችን እሁድ በይፋ በትረ ሥልጣኑን ከተሰናባቹ ፕሬዝደንት ፍራንሷ ኦሎንድ እንደሚረከቡ የተገለጸዉ አዲሱ የፈረንሳይ ፕሬዝደንት ማክሮ በሀገሪቱ የፖለቲካ ሜዳ ለረዥም ዓመታት የሚታወቁ ባይሆኑም መራጩ ሕዝብ ግን አዎንታዊ ተስፋ ሰንቆ እንደሚጠብቃቸዉ ነዉ የተገለጸዉ።
«ወጣት ፕሬዝደንት ናቸዉ፤ ከሦስት ዓመት በፊት አይታወቁም ነበር። እዚህ ፈረንሳይ እና በፖለቲካዉ ዉስጥ አንድ የተፈጠረ ነገር አለ፤ ያ ደግሞ ለእኛ ተስፋ የሰጠንና የሚያስደስት ነዉ፤ ተስፋ፣ በፖለቲካዉ ተስፋ። በጣም ደስ ይላል።»
«በጣም ብዙ ነገሮች ከእሳቸዉ እጠብቃለሁ። ሥርዓቱ ያቀረባቸዉ እጩ ሊሆኑ ይችላሉ ግን አፅናፋዊዉ ትስስር ሃቅ ነዉ። ራሳቸዉን እዚያ ላይ ከፍ አድርገዋል፤ ስለዚህ ይሁን፤ እሳቸዉንም እንሞክራቸዉ።»
የተለያዩ ሃገራት መሪዎች ለማክሮ የእንኳን ደስ ያልዎ መልዕክት መላካቸዉን ቀጥለዋል።