ፓሪስ፤ በሽብር ጥቃት የተገደሉት በአደባባይ ሠልፍ ታሰቡ
እሑድ፣ ጥር 3 2007በሠልፉ ከተገኙ መሪዎች መኻከል የፈረንሣዩ ፕሬዚዳንት ፍራንሷ ኦሎንድ፣ የጀርመን መራሒተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል፣ የእራኤል ጠቅላይ ሚንሥትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ፣ የፍልስጥዔሙ ፕሬዚዳንት፣ ሙሐሙድ አባስ፣ የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚንሥትር ዴቪድ ካሜሩን ይጠቀሳሉ። በሠልፉ የሩስያው የውጭ ጉዳይ ሚንሥትር ሰርጌ ላቭሮቭ፣ የዩክሬኑ አቻቸው ፔትሮ ፖሮሾንኮን ጨምሮ የ50 ሃገራት መሪዎች እና ከፍተኛ ባለሥልጣናትም ተገኝተዋል።
በርካታ የተለያዩ ተቋማት እና የፖለቲካ መሪዎች እንዲሁም የመገናኛ አውታሮች በሰልፉ መገኘታቸው ተጠቅሷል። በሠልፉ ውስጥ በየመኻከሉ «እኔም ሻርሊ ነኝ» የሚሉ መፈክሮች በተደጋጋሚ እየተሰሙ ነው። ሠልፉ ከፍተኛ ጥበቃ እየተደረገለት መሆኑም ታውቋል። በፓሪስ ሠልፉን ለመጠበቅ 2200 የሚጠጉ ፀጥታ አስከባሪዎች የተሰማሩ ሲሆን፤ አልሞ ተኳሾችም በከተማ ሕንጻዎች ላይ መስፈራቸው ተዘግቧል። እስካሁን በሽብር ጥቃት መታሰቢያሠልፉ ላይ ከ700.000 በላይ ሰዎች መሳተፋቸው ተገልጧል። ረቡዕ ዕለት «ሻርሊ ኤብዶ» የተሰኘው የስላቅ መፅሄት መሥሪያ ቤት ውስጥ ኹለት ወንድማማቾች እንዲሁም ሌላ አንድ ሰው የአይሁድ ሸቀጥ መደብር ውስጥ ባደረሱት ጥቃት 17 ሰዎች መገደላቸው ይታወሳል። አሸባሪዎቹ ከቀናት ክትትል በኋላ በፖሊሶች እንደተገደሉም ተዘግቧል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ልደት አበበ