ጎጂ ልማድ እንደ ባህል
ሐሙስ፣ ጥር 30 2005በዓለም ላይ በዛሬዋ ዕለት ምን አልባት በምላጭ አልያም በቢላዋ፣ በጠርሙስ ስባሪ ወይንም በቆርቆሮ ቁራጭ የተገረዘች ህፃን አትጠፋም። ከትውልድ ትውልድ ተላልፎ በመፈፀሙ አንዳንዶችም ባህላችን ብለው የሚጠሩት በሴቶች ላይ የሚፈፀም ግርዛት እንደ ቦታው ይለያያል።
«የተፈፀመው አንድ ፀጉር ቤት ውስጥ ነው። አንድ ቀን ወላጆች በሙሉ በሰፈሩ በእኔ እድሜ ክልል የነበሩ ልጃ ገረዶችን ሰብስበው ሰውየው ጋ ወሰዱን። እኛ ለምን እንደሆነ አላወቅንም ነበር። ደስ ብሎን ነበር። ምክንያቱም ለበዓሉ እጃችንን ሂና ተቀብተን ነበር በዛ ላይ የዶሮ ሾርባ ተሰጠን። በጣም ደስ ብሎን ነበር። »ትላለች ግብፃዊቷ ኡነ መሀመድ። ኡነ የ12 ሁለት አመት ልጅ ሳለች እንደሌሎች አብረዋት የነበሩት የሰፈሯ ልጆች ወንጀል ተፈፅሞባታል። ይህ ህመም ብቻ ሳይሆን በአዕምሮዋም ትቶ ያለፈው ነገር አለ።
« ለሶስት ቀናት እደማ ነበር። ታድያ ደጋግሜ ራሴን እጠይቀው የነበረው ነገር ቢኖር ምን ባጠፋ ነው ወላጆቼ ይህንን ያደረጉብኝ የሚል ነበር። አንዲት ልጅ እንደውም በዚህ የተነሳ ህይወቷ አልፏል።»ኡነ ብቻዋን አይደለችም። በአለም ዙሪያ ከ130-150 ሚሊዮን የሚሆኑ የሴት ልጅ ግርዛት ሰለባ መሆናቸው ይነገራል። አብዛኞቹ አፍሪቃ ውስጥ ናቸው። በአንዳንድ ሀገራት በህግ የሚያስቀጣ ሆኖም በ29 የአፍሪቃ ሀገራት የሴት ልጅ ግርዛት ይፈፀማል። ከነዚህ ሀገራት አንዷ ኢትዮጵያ ናት።
ጀርመን ውስጥም የሴት ልጅ ግርዛት ይፈፀማል። ፈፃሚ እና አስፈፃሚዎቹ ግን የውጭ ሀገር ዜጎች ናቸው። ማንም ይሁን ማን ድርጊቱ በጀርመን ህግም ያስቀጣል። ወላጆችም የማሳደግ መብታቸውን ያጣሉ። የቅጣቱ አይነት ይለያይ እንጂ ይህም በኢትዮጵያ መቅጫ ህግ ሰፍሯል። ለመሆኑ ህጉ ምን ያህል በተግባር ላይ ይውላል? በኢትዮጵያ በወቅቱ የሴት ልጅ ግርዛትን በተመለከተ ያለውንስ ሁኔታ ምን ይመስላል። ለዚህ እና ለሌሎች ጥቃቄዎች መልስ ለማግኘት የኢትዮጵያ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች አስወጋጅ ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ አሊ ሀሰንን አነጋግረናል።
ልደት አበበ
ተክሌ የኋላ