ጀርመናዉያን የሞቱበት የኢስታምቡሉ ጥቃት
ረቡዕ፣ ጥር 4 2008ማስታወቂያ
የሀገር ጎብኚዎች መነኻሪያ በሆነችዉ በታሪካዊቱ ኢስታንቡል ከተማ የ10 ጀርመናዉያን ጎብኚዎችን ህይወት የቀጠፈዉን ጥቃት ያደረሰዉ ራሱን እስላማዊ መንግሥት የሚለዉ ፅንፈኛ ቡድን አባል የሆነ የ28 ዓመት ሶርያዉ መሆኑም ተገልጿል። ትናንት በደረሰዉ ጥቃት ከሞቱት ሌላ 15 ሰዎችም ተጎድተዋል። አብዛኞቹ ጀርመናዉያን ሲሆኑ የኖርዌይ ዜጎችም እንደሚገኙበት ተገልጿል። የቱርክ የሀገር ዉስጥ ሚኒስትር ኢፍካን አላ ማንነቱ በዝርዝር ባይገለፅም ከጥቃቱ ጋር በተገናኘ አንድ ግለሰብ ትናንት ማምሻዉን መያዙን ዛሬ አስታዉቀዋል። ጉዳዩን በቅርበት ለመመርመር ወደዚያ የተጓዙት የጀርመን የሀገር ዉስጥ ሚኒስትር ቶማስ ደሚዜር፤ ምንም እንኳን የጥቃቱ ሰለባዎች ጀርመናዉያን ቢሆኑም፤ እነሱ ላይ ብቻ አደጋዉ እንዳነጣጠረ የሚያሳምን ነገር አለመኖሩን ተናግረዋል። በዚህ ምክንያትም ወደቱርክ ለመጓዝ ያቀዱ ጀርመናዉያን ሃሳባቸዉን መለወጥ እንደማያስፈልጋቸዉ አመልክተዋል። አንድ የታወቀ የጀርመን አስጎብኚ ድርጅት በበኩሉ ወደቱርክ ለመጓዝ የተመዘገቡ ደንበኞቹ ያለምንም ተጨማሪ ክፍያ የጉዞ አቅጣጫቸዉን ወደሌሎች ሃገራት መቀየር እንደሚችሉ ይፋ አድርጓል። የበርሊኑ ዘጋቢያችን ይልማ ኃይለሚካኤል ተከታዩን ዘገባ ልኮልናል።
ይልማ ኃይለሚካኤል
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ