ዶክተር አብይ አሕመድ ተመረጡ
ረቡዕ፣ መጋቢት 19 2010ማስታወቂያ
የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ምክር ቤት ዶክተር አብይ አሕመድን የግንባሩ ሊቀመንር አድርጎ መርጧል።ኢሕአዴግ ትናንት እኩለ ሌት ግድም በሰጠዉ መግለጫ ከሁለት ሳምንት በላይ የፈጀዉ የግንባሩ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ እና የምክር ቤት ስብሰባ በአግባቢ ሥምምነት ተጠናቅቋል።ከጥቂት ወራት በፊት የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ)ን የሊቀመንበርነት ሥልጣን የያዙት ዶክተር አብይ በፌደራልና በኦሮሚያ መስተዳድር በተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች ለበርካታ ዓመታት አገልግለዋል።በኢሕአዴግ አሰራር እና በኢትዮጵያ ሕግ መሠረት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ መቀመጫ ያለዉ ፓርቲ መሪ የሐገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር ይሆናል።በዚሕም መሠረት ዶክተር አብይ ሥልጣናቸዉን የለቀቁትን ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ተክተዉ የሐገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር ይሆናሉ ተብሎ በሰፊዉ ይታመናል።ላለፉት ሰወስት ዓመታት ኢትዮጵያን የሚያብጠዉን ሕዝባዊ ተቃዉሞ፤ ግጭት እና ፖለቲካዊ ቀዉስ ለማቃለል ያላቸዉ አቅም፤ ብልሐት እና ተቀባይነት ግን አሁንም አነጋጋሪ ነዉ።
ነጋሽ መሐመድ