1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ደቡብ ጎንደር በትግራይ ኃይሎች እጅ በቆየባቸው ጊዜያት ከ60 በላይ ሰዎች ተገድለዋል ተባለ

ቅዳሜ፣ ነሐሴ 29 2013

በአማራ ክልል የደቡብ ጎንደር ዞን በትግራይ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር በቆየባቸው ጊዜያት ከ60 በላይ ሰዎች መገደላቸውን የዳሰሳ ጥናት ያከናወኑ የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ባለሙያዎች ተናገሩ። ባለሙያዎቹ እንደሚሉት ከ1300 በላይ አባወራዎች አካባቢው በትግራይ ኃይሎች እጅ በቆየባቸው ጊዜያት የተለያዩ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

https://p.dw.com/p/3zvFd
Äthiopien Debretabor Universität
ምስል DW/A. Mekonnen

የደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ ባለሙያዎች ጉዳቱን የተመለከተ ጥናት ሰርተዋል

ህወሓት በደቡብ ጎንደር ዞን የተለያዩ አካባቢዎችን ተቆጣጥሮ በነበረበት ወቅት ከ111  ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የግለሰቦችን ንብረት መዝረፉንና ማውደሙን የጉዳት መጠኑን ያጠና ቡድን አስታወቀ፣ 120 ያህል ተቋማት ላይም ጉዳት ማድረሱን በደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ የተቋቋመ አጥኚ ኮሚቴ አመልክቷል፡፤

የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) በደቡብ ጎንደር ዞን የተለያዩ አካባቢዎችን ተቆጣጥሮ በቆየበት ወቅት በርካታ ዜጎችን ለችግር ዳርጎ መሄዱንበደብረታቦር ዩኒቨርሲቲየሰው ሀብትና የንብረት ውድመት አጥኚ ኮሚቴ አስተባባሪ ዶ/ር አምላኩ በላይ ዛሬ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል፡፡

በተለይ በግለሰብ ደረጃ በተጠቀሱ የዞኑ ከተሞች በሚኖሩ ግለሰቦች ላይ ከ111 ሚሊዮን 166 ሺህ 101 ብር በላይ የሚገመት ንብረት ዘርፏል ወይም አውድሟል ብለዋል፡፡
ከንብረት ውድመቱ በተጨማሪም ከ60 በላይ ንፁሀን በከባድ መሳሪያና በጥይት መገደላቸውን በጥነቱ መረጋገጡን ዶ/ር አምላኩ ገልፀዋል፡፡

በዩኒቨርሲቲው ሌላኛው የተቋማት ውድመት አጥኚ ኮሚቴው የደረሰበትን ውጤት አስመልክተው ዶ/ር አምላኩ እንዳመለከቱት 119 የግል፣ የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል፡፡

የወደሙ ንብረቶችን መልሶ ለመገንባት፣ በስነ ልቦና የተጎዱ ወገኖችን ለማጽናናትና የተቸገሩ ወገኖችን ለመደገፍ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣም አስተባባሪው ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ የሰው ሀብትናየንብረት ውድመት፣ እንዲሁም የተቋማት ውድመት እንዲያጠኑ በእያንዳንዳቸው 8 ሰዎችን ያካተተ ኮሚቴ አዋቅሮ ከነሀሴ 17 እስከ ነሀሴ 24 ጥናቱን አካሂዶ ትናንት ይፋ አድርጓል፡፡

ዩኒቨርሲቲው ቀደም ሲልም 10 ዩኒቨርሲቲዎችን አስተባብሮ ለነፋስ መውጫ ሆስፒታል መልሶ መቋቋሚያ 5 ሚሊዮን 5 መቶ ሺህ ብር የሚገመት ቁሳቁስና መድኃኒት እንዲቀርብ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ዓለምነው መኮንን

እሸቴ በቀለ