ደራሲ መዓዛ መንግሥቴና ሥራዎችዋ
ሐሙስ፣ መጋቢት 3 2012በዩናይትድ ስቴትስ ነዋሪ የሆነችዉ ትዉልደ ኢትዮጵያዊትዋ መዓዛ መንግሥቴ በቅርቡ በእንጊሊዘኛ ለአንባባን በአቀረበችዉ መጽሐፍ ላይ ሕዝባዊ ንግግሮችን እያደረገች ነዉ። ደራሲ መዓዛ መንግሥቴ በ1966 ቱ አብዮት ማግሥት ከወላጆችዋ ጋር ወደ ሃገረ አሜሪካ አቅንታ፤ እዝያዉ በዩናይትድ ስቴትስ የአደገች እና የተማረች ብሎም ታዋቂ ደራሲ እስከመሆን የደረሰች ትዉልደ ኢትዮጵያዊት ናት። መዓዛ በኒዮርክ ሲቲ ዩንቨርስቲ በሥነ-ጽሑፍ እና የልቦለድ አፃፃፍ ሞያ ተመርቃለች። በዝያዉ በኒዮርክ ዩንቨርስቲ የሥነ-ጽሑፍ መምርት ሆናም እያገለገለች ነዉ። መዓዛ በስደት እና ስደተኞች ላይ ያተኮሩ በርካታ አጫጭር ጽሑፎችን ላይ በተለያዩ ጋዜጦች ላይ እየፃፈች አስነብባለች። ደራሲ መዓዛ በጎርጎረሳዉያኑ 2010 ዓ.ም ይፋ ባደረገችዉ የእንጊሊዘኛ የመጀመርያ ልብወለድ መጽሐፍ አድናቆትን አግኝታለች። በኢትዮጵያ የአብዮቱ የመጀመርያ ዓመታት የነበረ አንድ የኢትዮጵያ ቤተሰብ ታሪክ ላይ የተመሰረተዉ ይህ ልብ ወለድ መጽሐፏ በበርካታ ሃያስያን እና ጋዜጦች ተደንቆአል። ዘ-ጋርድያን የተባለዉ የዜና አዉታር የደራሲ መዓዛ ልብወለድን ከአስር ምርጥ ልቦለድ ሰንጠረዥ ዉስጥ አስገብቶትም ነበር። ልቦለዱ ለበርካታ የሽልማት ዉድድርም በእጩነት ቀርቦ ነበር። ደራሲ መዓዛ ዛሬ በትዊተርዋ ይፋ እንዳደረገችዉ የአሜሪካዉ የሥነ-ጥበብ አካዳሚ የ 2020 ማለትም የዘንድሮ ለየት ያለ ስኬት ተሸላሚ አድርጎኛል ስትል ደስታዋን አካፍላለች። በብራስልስ የዶቼ ቬለ ወኪል ገበያዉ ንጉሴ በብራስልስ በተካሄደ አንድ የሥነ-ፅሑፍ ዝግጅት ላይ ደራሲ መዓዛ መንግሥቴን አግኝቶ አነጋግሮአታል።
ገበያዉ ንጉሴ
አዜብ ታደሰ