ደማስቆ፤ የሶሪያ የአየር ድብደባ
ረቡዕ፣ ኅዳር 5 2005የሶሪያ የጦር አውሮፕላኖችም ባለፈው ወር በአማፅያን ይዞታ ስር የወደቀውን ሰሜን ምዕራባዊውን ከተማ ማሬት አልኑማንን መደብደባቸውንም ድርጅቱ ዘግቧል ። በሌላ በኩል ፈረንሳይ ለሶሪያ መንግሥት ተቃዋሚ ቡድን እውቅና መስጠቷን ሶሪያ የጦርነት እወጃ ስትል አወገዘች ። ፈረንሳይ ቃትር ዶሃ ውስጥ ለተመሰረተው ለአዲሱ የተቃዋሚዎች ህብረት እውቅና በመስጠት የመጀመሪያዋ ምዕራባዊት ሃገር ናት ። የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ፍርንሷ ኦሎንድ ፓሪስ ለተቃዋሚዎቹ ህብረት እውቅና የሰጠችው እንደ ብቸኛው የሶሪያ ህዝብ ተወካይና የዲሞክራሲያዊት ሶሪያ የወደፊቱ ጊዜያዊ መንግሥት መሆኑን ተናግረዋል ። አማፅያኑን ማስታጠቅን በተመለከተም ወደፊት ለተቃዋሚዎች እውቅና ከሚሰጡ ሃገራት ጋር የሚታይ ነው ብለዋል የሶሪያ ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የዶሃውን ጉባኤ ጦርነት እወጃ ነው ፤ ተቃዋሚዎችም በተባበሩት መንግሥታት አሰራር ችግሩን በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ የማይፈልጉ ናቸው ብለዋቸዋል ።
ፈረንሳይም ለተቃዋሚው ብሄራዊ ህብረት እውቅና በመስጠት ገዳዮችንና ፣ አሸባሪዎችን በመደገፍ የሶሪያን ጥፋት ታበረታታለች ሲሉ ነቅፈዋል ። ፈረንሳይ ለተቃዋሚው ህብረት እውቅና ከሰጠች በኋላ ሩስያ ከተቃዋሚዎች ጎን የሚቆሙ ወገኖችን ተችታለች ። ሞስኮ በሶሪያ ጉዳይ በገልለተኛ አቋሟ እንደምትፀና ነው የተናገረችው ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በጦርነት ሰበብ የሚሰደዱት ሶርያውያን ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እያደገ ነው ። የሶሪያ ግጭት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ከሶሪያ የተሰደደው ህዝብ ቁጥር ወደ 700 ሺህ ይገመታል ። ከመካከላቸው አብዛኛዎቹ ሃገራቸውን ለቀው የወጡት ባዶ እጃቸውን ነው ። በዚህ የተነሳም ለችግር መዳረጋቸውን አንድ ግብፅ ውስጥ የተጠለሉ ሶሪያዊት ይናገራሉ ።
«ጦርነቱን ሸሽተን ነው የመጣነው ። ምንም ይዘን መውጣት አልቻልንም ። ለክረምቱ የሚሆን ልብስ አልያዝንም። »
ከሶሪያ ስደተኞች 300 ሺ የሚሆኑት ቱርክ ይገኛሉ ።