የፕሬዚዳንት አልሲሲ የሰሞኑ ዛቻና አንድምታው
ሐሙስ፣ መጋቢት 23 2013ማስታወቂያ
ኢትዮጵያ በመጪው ክረምት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውኃ ሙሌት እንደምታከናውን መንግሥት አሳውቋል። ይህንን ተከትሎ የግብፅ ፕሬዝዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ «የግብፅ ጠብታ ውኃ ከተነካ አካባቢው ቀውስ ያስተናግዳል» ሲሉ የመንግሥታቸውን አቋም አንፀባርቀዋል። ይህ የግብፅ አቋም አንድም የማስፈራራት ፣ በሌላ በኩል ከውኃ ሙሌቱ በፊት በኢትዮጵያ ላይ ጫና የማሳደር ዓላማ ያለው መሆኑን ያነጋገርናቸው ሁለት የዘርፉ አዋቂዎች ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በውስጥ አንድነቷ ፀንታ ሥራዋን መቀጠልና የሚመጣን ጫና መቋቋም ይገባልም ብለዋል ባለሙያዎቹ። በኢትዮጵያ ሱዳንና ግብፅ መካከል ሲደረግ የቆየው የረጅም ጊዜ ድርድር ከተቋረጠ ሰነባብቷል። የኢትዮጵያን ድንበር ጥሳ በመግባት ወረራ መፈፀሟ የተነገረው ሱዳንም ከግብፅ ጋር ወታደራዊ ልምምድ በማድረግ ድርድሩ እንዲጓተት እያደረገች መሆኑን የኢትዮጵያ መንግሥት ገልጿል። የኢትዮጵያ መንግሥት የግብፅ ፕሬዚዳንት ንግግር ላይ ግን እስካሁን ያለው ነገር የለም።
ሰለሞን ሙጬ
ታምራት ዲንሳ
ሸዋዬ ለገሠ