የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጋዜጣዊ መግለጫ በአዲስ አበባ
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 21 2007
ዴሞክራሲ ማለትም ምርጫ ማካሄድ ብቻ ሳይሆን ምርጫዉ ነፃ እና ፍትሃዊ መሆኑን ማረጋገጥ እንደሆነ የጠቆሙት ኦባማ የሕዝቦች ሀሳብን በነፃ የመግለፅና የመሰብሰብ ነፃነት እንዲሁም የፕረስ ነፃነትንም ያካትታል። ብለዋል። ፕሬዚዳንት ኦባማ ትናንትም ከኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በጋዜጣዊ መግለጫዉ ያነሷቸዉን አንዳንድ ነጥቦች በመጥቀስ የፖለቲካ ተንታኝ አነጋግረን ዝርዝር ዘገባ ይዘናል።
የልዕለ ኃያልዋ ሃገር ፕሬዚዳንት ዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ኢትዮጵያ ያስመዘገበችውን እድገትና በሶማሊያ አሸባብን ለመዋጋት የምታበረክተውን አስተቃጽዖ አድንቀዋል። ኢትዮጵያዉያን ጠንካራ ተዋጊዎች በመሆናቸዉም አሜሪካን ወታደሮቿን ሶማሊያ ዉስጥ ማሰማራት እንደማያስፈልጋት ነዉ የገለፁት። ኦባማ ኬንያ ካደረጉት ንግግር ይልቅ በኢትዮጵያ ቆጠብ ያሉ ይመሥላሉ ያሉት የፖለቲካ ተንታኝ ዩሱፍ ያሲን ኢትዮጵያ አሸባብን መዉጋትዋ የራስዋንም ፀጥታና ሰላምን ለማግኘት እንደሆነ ይገልጻሉ።
በትናንቱ ጋዜጣዊ መግለጫቸዉ ፕሬዚዳንት ኦባማ የኢትዮጵያ መንግሥት በዲሞክራሲ መንገድ የተመረጠ ነዉ ማለታቸዉ እንዴት ይገመገማል ለሚለዉ ጥያቄ የፖለቲካ ተንታኝ ዩሱፍ ያሲን እንድያም ሆኖ መቶ በመቶ የሚለዉን ማንም አያምንም ብለዋል።
ኦባማ በጋዜጣዉ መግለጫቸዉ ሃገራቸዉ በዲሞክራሲ የተመረጠን መንግሥት በኃይል ለመጣል የሚንቀሳቀስን ቡድን እንደምትቃወምም ተናግረዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ተቀማጭነቱን በዩኤስ አሜሪካ ያደረገ በኤርትራ የሚንቀሳቀስ የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚ ቡድንን የሃገራቸዉ የስለላ ድርጅት አሸባሪ ሲል አለመፈረጁንም ግልፅ አድርገዋል።
ፕሬዚዳንት ኦባማ በጋዜጣዊ መግለጫቸዉ የፖለቲካ ተቃዋሚዎች ድምፅ እንዲሰማ ጠይቀዋል። ሁሉም ድምፆች ሲሰሙ ሰዎች የፖለቲካ ሂደቱ አካል መሆናቸዉን ሲያዉቁ አንድ ሀገር ይበልጥ ጠንካራ ይበልጥ ስኬታማ ብቻ ሳይሆን የፈጠራ ችሎታም ይዳብራል ብዬ አምናለሁ ሲሉ የተናገሩት ኦባማ የፕረስ ነጻነት እንዲጠበቅም ጠይቀዋል።
በስልጣን ላይ ለመቆየት በእድሜ አላራጀሁም ሲሉ ዛሬ ለአፍሪቃ ሕብረት ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ለሶስተኛ ጊዜ ግን መመረጥ እንዳይችሉ ሕግ እንደሚያግዳቸዉ ገልጸዉ፤ የሀገራቸዉን ሕገ-መንግሥት በመቀያየር ሥልጣን የሙጥኝ ለሚሉ መሪዎች የአፍሪቃ ሕብረቱ ማዉገዝ እንዲለምድ መልዕክታቸዉን አስተላልፈዋል።
ጋዜጠኞች እየታሰሩ ዴሞክራስያዊ መንግስት አለ ብሎ መናገር እንደማይቻልም ሳይገልፁ አላለፉም። ሴቶችን ማሳደድና መድፈር ይቁም፤ ይህን ያደረገን መቅጣት ይኖርባችኋል ሲሉም ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ በንግግራቸዉ አስተጋብተዋል። ኢትዮጵያ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች የሚገኙባት በዓለም እንደምሳሌ የምትጠቀስ ሃገር መሆኗንም አስመረዉበታል።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ