የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዲስኩር በአፍሪቃ ህብረት
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 21 2007የአፍሪቃ መሪዎች የዴሞክራሲ ሥርዓትን እንዲያከብሩ፤ ሙስናን እንዲዋጉና ለዜጎቻቸዉ ሥራ እንዲፈጥሩ የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝደንት መከሩ። ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ ዛሬ አዲስ አበባ ዉስጥ ለአፍሪቃ ሕብረት አባል ሐገራት መሪዎችና ተወካዮች ባደረጉት ንግግር እንዳሉት፤ አፍሪቃ ከሁከት፤ አመፅና ግጭት የምትላቀቀዉ መሪዋችዋ ሕግና ደንብን ሲያከብሩ፤ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ሲገነቡ እና ለሕዝብ ፍላጎት ሲገዙ ነዉ።ኦባማ እንዳሉት አዲሲቱ አፍሪቃ እያጎነቆለች ነዉ።ይሁንና ጋዜጠኞች ሙያዊ ሐላፊነታቸዉን በመወጣታቸዉ ብቻ እየታሰሩ፤ የሲቢል ማሕበራት እየተደፈለቁ፤ የዴሞክራሲ ሥርዓት እየተገነባ ነዉ ማለት ሐሰት ነዉ-እንደ አሜሪካዉ ፕሬዝደንት እምነት።«ዲሞክራሲ መደበኛ ምርጫ ማለት ብቻ እንዳልሆነ ማስታወቅ አለብኝ።ጋዜጠኞች ምግባራቸዉን በማከናወናወናቸዉ ብቻ እየታሠሩ፤ መንግሥት በሲቢል ማሕበራት ላይ በሚወስደዉ እርምጃ ምክንያት አቀንቃኞች እየተዋከቡ፤ ዲሞክራሲ በስም እንጂ በገቢር አለ ማለት አይቻልም።መንግሥታት የሕዝባቸዉን መብት እስካለከበሩ ድረስ ሐገራት የነፃነትን ሙሉ ቃል ገቢር አድርገዋል ማለት አይቻልም።»
ኦባማ የአፍሪቃ መሪዎች የየሐገራቸዉን ሕግ ወይም ሕገ-መንግሥት እየጣሱ ዘመነ-ሥልጣናቸዉን ማራዘማቸዉን ኮንነዋል።ቡሩንዲን አብነት የጠቀሱት ኦቦማ አክለዉ እንዳሉት መሪዎች ወይም መንግሥታት በሥልጣን ላይ ለመቆየት ሲሉ ሕግ በጣሱ ቁጥር ዉጤቱ ግጭት፤ አመፅና ጥፋት ነዉ።
ነጋሽ መሐመድ
ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
አርያም ተክሌ
ሸዋዬ ለገሠ