የፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት በፎቶግራፍ አንሺዎች ዓይን
እሑድ፣ መስከረም 13 2011ፎቶግራፍን አስመልክቶ የሚነገር የአነጋገር ዘይቤ አለ። ይኸዉም አንድ ምስል ወይም ፎቶግራፍ ከአንድ ሺህ ቃላት በላይ ዋጋ እንዳለዉ ነዉ። ይህም አንድ ውስብስብ ሐሳብን በአንድ ምስል በብዙ አቅጣጫ ትርጉም ሊሰጥ ሊያስተላልፍ የሚችል ጥበብ ነው።
ዛሬ የተለያዩ የፎቶ ሙያዎች አሉ። ከነዚህም አንዱ የፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት ነዉ። የፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት ዜናዎችን ለመዘገብ ምስሎችን በካሜራ ከመሰብሰብ ጀምሮ አርትኦ ማድረግ እንዲሁም ለሕትመት ማብቃትን ሁሉ ያካትታል።
በኢትዮጵያ ዉስጥ በዚህ ሙያ ከሚሳተፉት ዉስጥ አንዱ ሙሉጌታ አየነ ጌቱ ይባላል። የአሶሽዬትድ ፕሬስ የፎቶግራፍ ወሊል ነዉ። ሙሉጌታ በፎቶ ጋዜጠኝነት ሞያዉ በአማካሪነት ከ«UNICEF» ጋር ይሰራል። የስራ ባልደረባዉ ታምራት ጌታቸዉ ደግሞ በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ የፎቶግራፍ ጋዜጠኛ ሲሆን ላለፉት 10 ዓመታት በዚህ ሙያ ማሳለፉን ይናገራል።
ፎቶግራፍ ማንሳት በራሱ ሥነ-ጥበብ እንደሆነ ባለሙያዎች ይከራከራሉ። ጆ ፕሉምሪጅ የተሰኘችዉ የታላቋ ብርታንያ ፎቶግራፍ ባለሞያ ፎቶ ማንሳት ሥነ-ጥበብ ነዉ በሚለዉ ሃሳብ ትስማማላች። እንደ ጆ ፕሉምሪጅ የሥነ-ጥበብ ባለሙያዎች ሥራቸዉ አንድን ሁኔታ ወይም ነገርን ጊዜ፤ ብርሃን እና ቦታን በመጠበቅ ለተመልካቾች ትርጉም እንዲኖረዉ አድርጎ በፎቶግራፍ ማቅረብ ነዉ።
ሙሉጌታ ክስተቶችን እየተከታተለ ታሪካ አዘል ፎቶግራፎችን በፕሮጀክት መልክ ያከማቻል። እንደ የትኛዉም ሙያ የፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት የራሱ ዉጣ ዉረዶች አሉበት። ሙሉጌታም ሆነ የስራ ባልደረባዉ ታምራት የሚስማሙት የፎቶግራፍ ማንሳት ክልከላ እንደ አንድ ዋና ተግዳሮት ነዉ። ይሁን እንጅ በአሁን ጊዜ፣ በተለይም መንግስት የፖለቲካ ለዉጥ እያደረኩ ነዉ ማለቱን ተከትሎ፣ በፎቶግራፍ ማንሳት ረገድም ክልከላዉ መጠነኛ መሆኑን ሙሉጌታ ተናግሮአል።
በፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት ሙያ ዉስጥ የፎቶግራፍ አንሽዉና በማህበረሰቡ መካከል ያለዉ ግኑኝነት ወይም አቀራረብ ወሳኝ ቦታ እንዳለዉ ሙሉጌታ ያምናል። በተለይ ፎቶግራፍ ከማንሳቱ በፊት የተነሽዉን ፍቃደኝነት መጠየቅ የሙያዉ ሥነ ምግባርም እንደሆነ ተናግሮአል።
ከኤርትራ የተመለሱትን የኦነግ አመራሮችን ለመቀበል በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ አዲስ አበባ፤ ፊንፊኔ ታድሞ እንደነበር ይታወሳል። በታዳሚዎች መካከል እንደነበር የሚናገረዉ ሙሉጌታ እሱ ያነሳዉን የአንድ ፈረሰኛ ወይም የ«አባፈርዳ» ፎቶግራፍ በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ላይ ከፍተኛ አድናቆት አትርፎለታል። ይህንኑ ፎቶግራፉን ለ«DW» አጋርቶአል። ስለተደነቀበት የ«አባፈርዳ» ፎቶግራፉ እንዲህ ነግሮናል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ