የፎልክስ ቫገን ሥራ አስኪያጅ ሥልጣን ለቀቁ
ረቡዕ፣ መስከረም 12 2008
በማጭበርበር ቅሌት ከፍተኛ ወቀሳ የተሰነዘርበት የጀርመኑ የመኪና አምራች ኩባንያ ፎልክስ ቫገን ዋና ስራ አስኪጅ ማርቲን ቪንተርንኮርን ዛሬ ሥልጣን ለቀቁ ።ስራ አስኪያጁ ኩባንያቸው ላደረሰው ጥፋት ትናንት በይፋ ይቅርታ ጠይቀው ነበር ። ይሁንና ይቅርታ በጠየቁበት መልዕክታቸው ትልቁን የአውሮፓ መኪና አምራች ኩባንያ ከመምራት ሃላፊነታቸው የመውረድ ፍንጭ አላሳዩም ነበረ ። ዛሬ የፎልክስ ቫገን የቦርድ አባላት በቅሌቱና በኩባንያው የወደፉት እጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር ተሰብስበው ነበር ።ስራ አስኪያጁ ሥልጣን መልቀቃቸው የተነገረው በስብስባው መሃለ ነበር ።በሌላ በኩል የጀርመን አቃቤ ህግ ፣በፎልክስ ቫገን የማጭበርበር ቅሌት ላይ የመጀመሪያ ደረጃ የወንጀል ምርመራ መጀመሩን አስታወቋል ። የብሩንስቪክ አቃቤ ህግ ፎልክስ ቫገን በናፍጣ በሚሰሩ መኪናዎች ላይ የተጭበረበረ የአየር ብክለት መቆጣጠሪያ ስለ መግጠሙ በኩባንያው የአስተዳደር ሃላፊዎች ላይ ምርመራ ለማካሄድ ማሰቡን ተናግረዋል ።ቪንተርንኮርን ኩባንያቸው ያጋበሰው ትርፍ ተጠቃሚ ሊሆኑ እንደሚችሉ ግልጽ ነው ይላሉ በአሜሪካው የካርኔጅ የጥናትና በጎ አድራጎት ተቋም የመኪና ሞተር ጉዳዮች አዋቂ ዴቦራ ጎርደን
« ፎልክስ ቫገን ባለፉት ዓመታት እየተስፋፋና ገቢውም እየጨመረ ሲሄድ በተለይ እርሳቸው ያገኙትን ጥቅምና የተጋሩትን ለይቶ ማወቁ ለፍትህ ሚኒስቴር ቀላል ነው ። ይሄ በኩባንያዎች አሠራር ውስጥ የተለመደ ነው ።»
። 11 ሚሊዮን የሚደርሱ በናፍታ የሚሰሩት መኪናዎቹ የብክለት ምርመራን ማለፍ የሚያስችል የተጭበረበረ ሶፍትዌር እንደተገጠመላቸው ያመነው ከዓለም ግዙፉ የመኪና አምራች ፎልክስ ቫገን ከፍተኛ የህግ መጣስ ክሶች እንደሚጠብቁት ይገመታል ። የአሜሪካን የአካባቢ ጥበቃ መሥሪያ ቤት በኩባንያው ላይ የ18 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ሊያስከትል የሚችል ምርመራ በማካሄድ ላይ ነው ።
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሀመድ