የፌስቡክ አብዮት ሲፈተሽ
ሰኞ፣ ሚያዝያ 29 2004በሰሜን አፍሪቃ ከተካሄደዉ አብዮት ወዲህ፤ ፌስ ቡክ፣ ትዊተር እና ብሎግ የተሰኙት የኢንተርኔት ማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች፤ ህዝባዊ አመፅን ለማቀጣጠል የሚችሉ የብዙሃን መገናኛዎች እንደሆኑ ታይቷል። «አብዮቱ ከፈነዳ በኋላ ኢንተርኔት አንዱ የአመፅ ማቀጣጠያ እንደነበር ታይቷል። ይሁንና ዲሞክራሲን ለመገንባት ሌላ ስልት ያስፈልጋል» ይላል ግብፃዊው ታሬክ አምር። የኢንተርኔት አምደኛው አምባ ገነኑ ሙባረክ ከስልጣን ሲወርዱ ተከታትሏል። ለለውጡም የበኩሉን አስተዋፅዎ በዚሁ በኢንተርኔት አማካኝነት አድርጓል። አምር በበርሊን ከተማ ዶይቸቬለ ባዘጋጀዉ የአምደኞች ስብሰባ ላይ ተካፍሏል። ስብሰባው የቴክኖሎጂ አድናቂዎችና ተጠቃሚዎቹን ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ አቋማቸዉን ያንፀባረቁ እንግዶችም አሳትፏል።
በቱኑዚያ የታየዉን ተከትሎ ብዙዎች የፌስቡክ አብዮት ሲሉ ይደመጣል፤ ለመሆኑ እንዴት ነው ኢንተርኔት ፓለቲካን የለወጠው? የፖለቲካ ሂደቱስ በኢንተርኔት እና በመገናኛ ብዙኃን ምን ይመስላል? የሚሉ ጥያቄዎችን በማንሳት የዶይቸ ቬለ አወያይ ሮበርት ሙጄ ግብፅን፣ ቱኒዚያንን እና ሶሪያን እንደምሳሌ ጠቅሷል።
ሶስቱ አገሮች የተለያዩ እንደመሆናቸው መጠን የመገናኛ ብዙኃን አቀራረቡም የተለየ ነው። ምንም እንኳን ኢንተርኔት ለዲሞክራሲ መስፈን በቀጥታ መፍትሄ ማግኛ ስልት ባይሆንም፤ በትዊተር እና ፌስ ቡክ አማካኝነት ማንኛውም ዜጋ እንደጋዜጠኛ የሰጣቸው መረጃዎች ዛሬም አብዮቱ ከፈነዳ በኋላ አላቆሙም ትላለች «ዓለም ዓቀፍ ድምፆች» ከተሰኘዉ ዓለም ዓቀፍ የአምደኞች ጥምረት ጋዜጠኛ ክሌር ዑርሊሽ። ይበልጥ ያተኮረችዉ ቱኒዚያ ላይ ሲሆን፤ «ቀደም ባለዉ ጊዜ መገናኛ ብዙኃን የሚመሩት ስልጣን ላይ ባለዉ አካል ነበር። አሁን ግን ሐገሪቱ ወደሌላ አቅጣጫ ያዘነበለችበት ሁኔታ ነው ያለው» ባይ ናት። ዑርሊሽ አበረታች ካለቻቸዉ ነጥቦች አንዱ፤ አንዳንድ ከተሞች ከኅብረተሰቡ ጋዜጠኞችን ለማፍራት ለወጣቶች የጋዜጠኝነት ሙያ ስልጠና መስጠታቸዉን ነው። እናም «ማን ያውቃል አንድ ቀን እነዚህ የኢንተርኔት ተጠቃሚ ተሟጋቾች አዲስ የቱኒዚያ ጋዜጣ አሳታሚዎች ይሆኑ ይሆናል» ነው ያለችው።
በሶሪያ መገናኛ ብዙኋን አሁንም በመንግስት እጅ ይገኛሉ። ሶርያዊቱ የኢንተርኔት አምደኛ ሌኢላ ናሃቫቲ መገናኛ ብዙሃኑ ካለዉ እዉነታ ተቃራኒዉን ይዘግባሉ በማለት « በአገሪቱ ምንም እንዳልተፈጠረ በመንገድ ላይ አይስክሬም የሚልሱ ሰዎችን በቴሌቪዥን ያሳያሉ» ስትል ትገልፃቸዋለች። አንዳንዴም የፈጠራ መሆናቸዉ የተነቃባቸዉን የሽብር ጥቃቶች ደጋግመዉ እንደሚያሳዩ ስታስረዳ ደግሞ «ሰዎችን ቁስለኛ ናቸዉ በሚል ያሳዩና፤ ትንሽ ቆይተው ሰዎቹ ቆመው ሲሄዱ ይታያሉ። ይህ ከእውነታ የራቀ ነው» ትላለች። በአምደ መረብ በሚቀርቡት ያለዉን ችግር ስትገልፅ « ብዙዎቹ የኢንተርኔት መረጃ አስተላላፊዎች አንድ የተቃውሞ ሰልፍ ወይም የቀብር ስነ ስርዓት ሲካሄድ በቀጥታ እየቀረፁ እንደሚያሳዩ፤ የትኛው ትክክል የትኛው ሃሰት እንደሆነ ለመለየት እንደሚያዳግት አመልክታ፤ ችግሩ ግን የእነሱ ሳይሆን የውጭ አገር ጋዜጠኞችን ወደ አገሩ ማስገባት የማይፈልገዉ የአገሩ መንግዕስት ነው፤» ትላለች።
በዉይይቱ ላይ የተገኙት አምደኞች ኢንተርኔት በህዝባዊዉ አመፅ እንቅስቃሴ ላይ የተጫወተዉን ታላቅ ሚና በእርግጠኝነት ይናገራሉ። ናሃቫቲ የኢንተርኔት መረጃ ልዉዉጡ «የአመፁን አንቀሳቃሽና ተሟጋቾች ከአገሪቱ አንድ ጫፍ እስከሌላኛው አገናኝቷል» ሲል፤ ታሬክ አምር ደግሞ «ቲኒዚያዎች ለእኛ ለግብፃዊያን ተስፋ ሰጥተዉናል» ይላል።
ልደት አበበ