የግሪክ ብድር መዘዙና መፍትሄው
ማክሰኞ፣ የካቲት 3 2007
ከሁለት ሳምንት በፊት ሥልጣን የያዘው አዲሱ የግሪክ መንግሥት ለህዝቡ በገባው ቃል መሠረት በግሪክ እዳና ብድር ላይ ከአበዳሪዎች ጋር እንደራደደር በሚለው ሃሳቡ ገፍቷል ። የግራ መስመር ተከታይ የሆነው የሲሪዛ ፓርቲ መሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አሌክሲስ ሲፕራስ ግሪክ በገንዘብ ቀውስ ውስጥ በተዘፈቀችበት ወቅት 240 ቢሊዮን ዩሮ ብድር ሲሰጣት በተስማማችበት የኤኮኖሚ ማሻሻያ ውስጥ የተካተተውን የበጀት ቅነሳ አስቀራለሁ ሲሉ የገቡትን ቃል በተግባር ለመተርጎም እየጣሩ ነው ። እርሳቸውና አዲሱ የገንዘብ ሚኒስትር ያኒስ ቫሩፋኪስ ካለፈው ሳምንት አንስቶ በተለያዩ የአውሮፓ ሃገራት እየተዘዋወሩ አዲሱን ሃሳባቸውን ለማሰመን በመሞከር ላይ ናቸው ።ይሁንና ይህ የግሪክ መሪዎች ጥያቄ እስካሁን በጎ ምላሽ አላገኘም ። ዋነኛዎቹ አበዳሪዎች ግሪክ ከዚህ ቀደም በተስማማችው መሠረት የአውሮፓ ሕብረት የአውሮፓ ማዕከላዊ ባንክና የዓለም የገንዘብ ድርጅት ባወጡት የኤኮኖሚ ማሻሻያ እንድትቀጥል እዳዋንም እንድትከፍል እያሳሰቡ ነው ። ግሪክንና አበዳሪዎቿን የሚያያስማማ አዲስ መፍትሄ ለጊዜው ባይገኝም ግሪክ ግን ኤኮኖሚየን ሊያሳድግ ይችላል ያለችውን አዲስ እቅድ አውጥታለች ። በርሊን ነዋሪ የሆኑት የኤኮኖሚ እድገት መምህርና ተመራማሪ እንዲሁም የኤኮኖሚ ጉዳዮች አማካሪ ዶክተር ፈቃዱ በቀለ የእቅዱን ምንነት ይገልጹልናል ።
አዲሱ የግሪክ መንግሥት አስቀራለሁ የሚለው በአበዳሪዎች የተጫነበት የበጀት ቅነሳና የቁጠባ እርምጃ በዶክተር ፈቃዱ አስተያየት ግሪክን የኤኮኖሚ ቀውስ ውስጥ ከከተቷት ዋነኛ ምክንያቶች አንዱ ነው። ዶክተር ፈቃዱ እንደሚሉት በነዚህ ርምጃዎች ግሪክ ተጠቃሚ ሳትሆን የበይ ተመልካች ነው የሆነችው ።
በግሪክ የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተባለው መርሃ ግብር ተግባራዊ ከሆነ በኋላ በሃገሪቱ የሥራ አጡ ቁጥር ከ12 በመቶ ወደ 25 በመቶ ከፍ ብሏል ።ድህነቱም ከፍቷል ። እስካሁን ተግባራዊ የሆኑት የኤኮኖሚ ፖሊሲዎች ኤኮኖሚውን ከማሳደግ ይልቅ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ከተውታል ይላሉ ዶክተር ፈቃዱ ።ታዲያ ሃገሪቱ ከነዚህ ማብቂያ ከታጣላቸው ችግሮች እንዴት መላቀቅ ትችል ይሆን? ዘላቂው መፍትሄስ ምንድን ነው የሚሆነው?
እስካሁን ለሚያወዛግበው ለግሪክ የኤኮኖሚ ችግር በመፍትሄነት ከሚቀርቡት ሃሳቦች አንዱ ግሪክ ከዩሮ አባልነት ትውጣ የሚል ነው ። ይህ አማራጭ መፍትሄ ሊሆን ይችላል ተብሎ ቢገመትም ለግሪክም ይሁን ለሌሎች የዩሮ ዞን አባል ሃገራት ጉዳት ማስከተሉ አይቀርም እንደ ዶክተር ፈቃዱ ።
ከዚህ ሌላ ግሪክ አሁን ያነሳችው ጥያቄ የቁጠባ እርምጃዎችን ተግባራዊ ካደረጉ ሌሎች የዩሮ ተጠቃሚ አባል ሃገራትም በኩል ሊነሳ ይችላል የሚል ስጋት አለ ። ይህ ደግሞ ለጋራው መገበያያ ገንዘብ ዩሮ አደጋ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል ።
ኂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ