1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋዜጠኞች ግድያ በሶማሊያ

ሰኞ፣ ነሐሴ 7 1999

የሶማሊያ ታጣቂዎች የሶማሊያ ጋዜጠኞች በአሁኑ ሰዓት እጅግ በከፋ ሁኔታ ውስጥ ነው የሚሰሩት ።

https://p.dw.com/p/E0YD
ምስል AP
የሶማሊያ ጋዜጠኞች በሀገሪቱ በሚንቀሳቀሱ የተለያዩ የፖለቲካ ቡድኖች የጥቃት ዒላማ ውስጥ መግባታቸው እየተባባሰ መምጣቱን የሶማሊያ ጋዜጠኞች ህብረት አስታወቀ ። የህብረቱ ዋና ፀሀፊ ኦማር ፋሩክ ኦስማን ለዶይቼቬለ ራድዮ የአማርኛው ክፍል እንደተናገሩት የሶማሊያ ጋዜጠኞች በአሁኑ ሰዓት እጅግ በከፋ ሁኔታ ውስጥ ነው የሚሰሩት ። አሊ ኢማን ሻርማርኬ ሆርን አፍሪክ የተባለው የግል የመገናኛ ብዙሀን ቡድን መሪ እና ማሀድ አህመድ ኤልሚ የሆርን አፍሪክ ንብረት ከሆኑት ሁለት ራድዮ ጣቢያዎች የአንዱ ሀላፊ ከትናንት በስተያ ነበር በተለያዩ ሁኔታዎች የተገደሉት ። የሶማሌ እና የካናዳ ዜግነት ያለው አሊ ሻርማርኬ ከባልደረባው ከማሀድ ኤልሚ ቀብር ሲመለስ ነበር መንገድ ላይ በተወረወረ ቦንብ የተገደለው ኤልሚ ደግሞ ወደ ስራው በመሄድ ላይ ሳለ ቅዳሜ በሁለት ታጣቂዎች ተተኩሶበት ነው የሞተው ። ባለፈው ቅዳሜ የተገደሉትን እነዚህን ሁለት ጋዜጠች ጨምሮ ከጥር ወር ወዲህ በሶማሊያ የሞቱት ጋዜጠኞች ቁጥር ስድስት ደርሷል ። የሶማሊያ ጋዜጠኞች ህብረት ዋና ፀሀፊ ኦማር ፋሩክ ኦስማን ለዶይቼቨለ ራድዮ የአማርኛው ክፍል እንዳሉት የሶማሊያ ጋዜጠኞች አሁን እጅግ አስቸጋሪ ወቅት ላይ ነው ያሉት ። ህዝቡን በማገልገላቸው ልዩ ልዩ ዓላማዎችን የሚያራምዱት የፖለቲካ ቡድኖች ኢላማ ውስጥም እየገቡ ነው ።
ድምፅ
«ጋዜጠኞችና የመገናኛ ብዙሀን ባልደረቦች የጥቃት ዒላማ ውስጥ የሚገቡት በሚፅፉትና በሚናገሩት ለህዝብ በሚሰጡት አገልግሎት ነው ። እነዚህ ጋዜጠኞች ደግሞ ጥቃት የሚደርስባቸው ከተለያዩ የፖለቲካ ቡድኖች ነው ። አንዳንድ የፖለቲካ ቡድኖች መረጃዎች ከራሳቸው ጥቅም አንፃር ብቻ እንዲተላለፉ ነው የሚፈልጉት ። እነርሱ የሚፈልጉት መረጃ ዋጋ ካልተሰጠው ጋዜጠኞችን ለማጥቃት ይሞክራሉ ። »
እንደ ሶማሌ ጋዜጠኞች ህብረት ዋና ፀሀፊ ኦማር ኦስማን ከሆነ ጋዜጠኞች የጥቃት ሰለባ የሆኑበት የሆኑበት ሌላም ምክንያት አለ ።
«መቅዲሾ አደገና ናት፣ ፀጥታዋ አያስተማምንም በሶማሊያ ሁኔታዎች ከቀድሞው ተባብሷል የሚል ምልክት ማስተላለፊያም እየተደረጉ ነው ጋዜጠኞች ። ምክንያቱም ጋዜጠኛን መግደል የመገናኛ ብዙሀን ባልደረባን መግደል ፣ መገናና ብዙሀንን ማጥቃት ዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ በቀላሉ ሊሰማው የሚችል ነገር ነው ። ጋዜጠኞች የጥቃት ሰለባ የሚሆኑበትም አንዱ ምክንያት ይሄ ነው ። »
ኦማር ኦስማን እንደሚለው በአውሮፓውያኑ ሁለት ሺህ ሰባት ከሞቱት ስድስት ጋዜጠኞች ሌላ ባለፈው ቅዳሜ ሁለት ቆስለዋል ። ሀገሪቱም ወደ ከፋ የፀጥታ ችግር ውስጥ ገብታለች ።
«ይሄ እጅግ አሳዛኝና አስደንጋጭ ነው ። አገሬ ትንሿ የአፍሪቃ ኢራቅ ሆናለች ። ይህም ለሶማሊያ የመገናና ብዙሀን ውንድሞቻችን አሳዛኝ ዜና ነው ።
ይሁንና እንደ ሶማሌ ጋዜጠኞች ህብረት ዋና ፀሀፊ የሀገሪቱ ጋዜጠኞች በዚህ ተስፋ ሳይቆርጡ ጠንክረው መቆም ነው ያለባቸው ።
«የሶማሊያ ጋዜጠኞች መጠንከር መቁረጥና ከጋዜጠኝነት ሙያቸው አለማፈግፈግ ነው የሚፈለግባቸው ህዝቡን ለማገልገል ለህዝቡ መስዋዕትነት ለመክፈል ፈተናዎችን መጋፈጥ አለባቸው መብታቸውን ማስጠበቅ መተባበር አለባቸው ። ሌላው አስፈላጊ ጉዳይ ከሶማሊያ ህዝቦች እንዲሁም ከዓለም ዓቀፍ ማህበረሰብ በኩልም አስፈላጊውን ትብብር ማግኘት ይገባል ። ፈተናውን ለማለፍና የሶማሌ ህዝብና ዓለም ዓቀፍ ማህበረሰብ ጋዜጠኞችና በአጠቃላይ የመገናኛ ብዙሀን ባለሞያዎች ወንጀል በሚፈፅሙት ወንጀለኞች ላይ የጋራ ግንባር መፍጠር አለባቸው ። »
በኦማር ፋሩክ ኦስማን የሚመራው የሰማሌ ጋዜጠኞች ህብረት አሜሪካን ውስጥ የሚገኘው የጥቁር ጋዜጠኞች ብሄራዊ ማህበር በየዓመቱ የሚሰጠውን የፕሬስ ነፃነት ሽልማት ባለፈው ሀሙስ ተሸልሟል ።