1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን የአፍሪቃ ፖሊሲ

ሐሙስ፣ መጋቢት 11 2006

አፍሪቃ ዉስጥ የጀርመንን ጣልቃ ገብነት የሚጋብዙ በየሳምንቱ የሚቀሰቀሱ አዳዲስ ቀዉሶች ሳይጠቀሱ አያልፉም። ለአብነት ያህል ሶማሊያ፣ ማሊ፣ ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፑብሊክን መጥቀስ ይቻላል።

https://p.dw.com/p/1BTSq
Bundeswehr Airbus am 14.04.2013 in Bamako Mali
ምስል Sebastian Wilke/Bundeswehr

በአዲሱ የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር የኃላፊነት ዘመንም ከስድስት በማያንሱ ዘርፎች ማለትም በመከላከያ፣ በልማት ርዳታ፣ በኤኮኖሚ፣ በግብርና፣ በዉስጥና በዉጭ ጉዳዮች የጀርመን አፍሪቃ ፖሊሲ በአዲስ መልኩ እንዲቀጥል ታቅዷል።

የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር በሚቀጥሉት ቀናት ሶስት የአፍሪቃ ሃገራትን ይጎበኛሉ። በቅድሚያ ወደኢትዮጵያ የሚያቀኑት የጀርመን ባለስልጣን አዲስ አበባ ላይ ከአፍሪቃ ኅብረት ባለስልጣናት ጋም እንደሚነጋገሩ ተገልጿል። በቀጣይም ታንዛኒያ እና አንጎላን ይጎበኛሉ።
«የተረሳችዉ ክፍለ ዓለም» ማለትም አፍሪቃ እጅግም በበርሊን ፖለቲካ ዉስጥ አልነበረችም፤ ሌሎቹ ከቱርክ አንስቶ እስከ ሕንድ ድረስ እዚያ ተገኝተዉ የየራሳቸዉን ስልት ሲያካሂዱ ጀርመኖች ረስተዋት ቆይተዋል። እንዲያም ሆኖ ባለፉት ዓመታት በተደጋጋሚ ወቅታዊ ቀዉሶች ወይም ከቻይና ጋ አፍሪቃን መቀራመት በሚለዉ ርዕዮተ ዓለም፤ አፍሪቃን የሚመለከቱ ስልታዊ ጥናቶች ከየጠረጴዛዉ ጠፍተዉ አያዉቁም። ግን በፍላጎት ማጣት ወይም ጣልቃ ገብነትን በሚሸሸዉ መመሪያ ምክንያት አቧራ ወርሷቸዋል።
ማሊ ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፑብሊክ ሶማሊያ,,,, በየሳምንቱ ለወደፊት ጀርመንን እዚያ ሊያሳትፍ የሚችል ቀዉስ አፍሪቃ ዉስጥ ሳይነሳ ያለፈበት ጊዜ ያለ አይመስልም። የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሽታይንማየር አዲሱ የአፍሪቃ ፖሊሲ ደግሞ መከላከያ፣ የልማት ርዳታና የኤኮኖሚ ግንኙነትን ጨምሮ ከስድስት የማያንሱ ዘርፎች ላይ ለማተኮር ያለመ ይመስላል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ጀርመን ከአጎራባቿ ክፍለ ዓለም ጋ ግንኙነቷን ለማጠናከር ያነሳሳት የቢሊዮኖች መኖሪያ የሆነችዉ አፍሪቃ ለወጪ ምርቶቿ ዋና መዳረሻ ገበያ ትሆናለች በሚል፤ ወይም ደግሞ የአሸባሪዎች የግንኙነት ሰንሰለት ከሶማሊያ ወደማሊ ተዘርግቷል በሚለዉ ስጋትም አይደለም። በፍፁም። ይልቁንም አዲሱ የጀርመን አፍሪቃ ፖሊሲ ያነቃቃዉ የፈረንሳይ የአፍሪቃ ፖሊሲ መሆኑ እዉነታዉ። ጀርመን በሰሜን ማሊ እና በማዕከላዊ አፍሪቃ ሬፓብሊክ ውስጥ ተልዕኮዎች ያሳየችው አዝጋሚነት ፓሪስን ቅር አሰኝቶዋል። በጀርመን የባደን ቩርተምበርግ ግዛት የነበረው የጀርመንና የፈረንሳይ ወታደራዊ ብርጌድ ባለፈዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2013 የመፀዉ ወራት ላይ የተበተነውም እንዲያው ያጋጣሚ ጉዳይ አልነበረም። ጀርመን በማሊ እንዲሁም በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፑብሊክ ለሚካሄደዉ ዘመቻ ወጪ እንዲመደብና የቀረበውን ሀሳብ ውድቅ ያደረገችበትም ውሳኔዋ የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ይበልጡን አሻክሮዋል። እንዲያም ሆኖ በአፍሪቃ ወታደራዊ ስልጠና ለመስጠት ጀርመን ያሳየችዉ ፈቃደኝነት እና ከየካቲት አጋማሽ አንስቶ የፍራንኮ ጀርመን ብርጌድን ወደማሊ እንዲሄድ ያሳለፈችው ትዕዛዝ ለፓሪስ የሚያመላክተዉ ነገር አለ።
ነገር ግን በአዲሱ የጀርመን የአፍሪቃ ፖሊስ በትክክል ምን ዓይነት መልዕክት ነዉ ማስተላለፍ የተፈለገዉ? ተጓዳኞች ተዋጊ ወታደሮች ይፈልጋሉ፣ የመከላከያ ሚኒስትሮች የሕክምና አዉሮፕላን፣ የልማት ሚኒስትሮች ደግሞ የእርስ በርስ ግጭቶችን መከላከያ ይሻሉ። አፍጋኒስታን ዉስጥ የተከሰቱትን በርካታ ግጭቶች የሚያስታዉስ፣ አዲሱ የአፍሪቃ ፖሊሲ በተለያዩት የሥልጣን ዘርፎች መካከል በሚካሄደው ፉክክር የተነሳ በጥንቃቄና በትክክል መከናወኑን በስጋት ነዉ የሚመለከተዉ።

የአዉሮጳን ፖሊስ በአፍሪቃ ጫንቃ ላይ ለመጫን መሞከር አደገኛ ነዉ፤ በርሊንም የማትጠብቀውን ቃል ከምግባት መቆጠብ ይኖርባታል። አጋሮችዋ ወታደሮቿን ለጦር ተልዕኮ ዝግጁ እንድታደርግ ከጠየቁ፣ ይህ ግንኙነታቸውን የሚያቀዘቅዝበትን ሁኔታን እንዳያፈጥር ያሰጋል። ምክንያቱም ይህን በርሊንም ሆነች ፓሪስ ሳይሆኑ ቩፐርታል ናት የምትወስነውና። በቩፐርታል እና በሌሎች የጀርመን ክፍሎች ይህን አስመልክቶ በተሰባሰበ የሕዝብ ድምፅ አብዛኛዉ ዜጋ የጀርመንን ወታደራዊ ተልዕኮ ማስፋፋት ተቃዉሟል።

Äthiopien Semara Straßenbau
ምስል DW/G.-T.Haile-Giorgis
Steinmeier EU Sanktionen Krim Referendum 17.3.2014 Brüssel
ምስል picture-alliance/dpa

ሉድገር ሻዶምስኪ

ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ