የጀርመን ክለቦች ድልና የአዉሮጳ ሊግ
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 3 2005
የዘንድሮዉ የአዉሮጳ የእግር ኳስ ክለቦች ግጥሚያ (ሻምፒዮንስ ሊግ) በሊጉ የእስካሁን ታሪክ ያልታዩ አዳዲስ ክስተቶች እየታዩበት ነዉ።ለረጅም ዘመን የሻምዮን ሊጉን ግጥሚያ የሚመሩት የኢንግላንድ፥ የፈረንሳይና የኢጣሊያ ክለቦች እየተንጠባጠቡ የስጳኝና የጀርመን ክለቦች ጥንካሬያቸዉን እያሳስመሰከሩ ነዉ።የስጳኞቹ ሪል ማድሪድ እና የጀርመኖቹ ባየር ሙዉኒክ እና ቦሪያሲያ ዶርትሙድ ተጋጣሚዎቻቸዉን እያሰናበቱ ለግማሽ ፍፃሜ ደርሰዋል።ጀርመን በአዉሮጳ ሻምፒዮን ሊግ ሁለት ቡድናት ሥታሰልፍ ያሁኑ የመጀመሪያዉ ነዉ።
እግር ኳስ አገሩ ገባ (ፉት ቦል ካም ሆም) ብሎ ቡረቃ ዘንድሮ ኢንግላንድ ላይ የለም።በአዉሮጳ ሻምፒዮን የእስከ ዘንድሮ ኮኮቦች የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ ቡድናት እዚያዉ እንግሊዝ ናቸዉ።ፈረንሳዮች ፓሪስ ላይ ጮቤ ለመርገጥ የቀራቸዉ አንድ ተስፋ ነበር።ፓሪስ ሳ ዠርሜ።-ካታላኖች አሰናበቱት።
የማላጋዎች ተስፋ በዶርትሙንዶች ቢመክን ስጳኞች ከአንድም ሁለት አማራጭ አላቸዉ።የካታላኖቹ ባርሴሎና፥ ወይም ሪል ማድሪድ።ኢጣሊያዎችም፥ ጆቬንቱስ ቱሪኖን ተመኝተዉ ነበር።ባየር ሙኒኮች ትናንት በምኞት አስቀሩባቸዉ።የባየር ሙዉኒኩ ፕሬዝዳት ኡሊ ሆነስ እንዳሉት የአዉሮጳ አንደኞች እንግሊዞች፥ ኢጣሊያዎች፥ ወይም ፈረንሳዮች አይደሉም።ስጳኝ ወይም ጀርመኖች እንጂ።
«ባሁኑ ጊዜ የጀርመን እና የስጳኝ እግር ኳስ (ክለቦች) ከአዉሮጳ አንደኛ መሆናቸዉ ምንም ጥር ጥር የለዉም።»
ከሪል ማድሪድ ይልቅ ባርሴሎና፥ ከባየር ሙዉኒክ ይበልጥ ቦርሲያ ዶርትሙንድ ለግማሽ ፍፃሜ ያለፉበት መንገድ ከእግር ኳስ ጥበብ፥ ጥንካሬ፥ ከየተጋጣሚዎቻቸዉ ድክመት እኩል እድል የተቀየጠበት ነበር።ባርሴሎና-ለግማሽ ፍፃሜ የደረሰዉ ከፓሪስ ሳ ዠርሜ ጋር በደርሶ-መልስ ግጥሚያ የጎል ብዛት ቆጥሮ፥-ቦሪሲያ ዶርትሙንድ ደግሞ የማላጋን ክለብ በባከነ-ሠዓት ባስቆጠረዉ ግብ በልጦ ነዉ።ለኡሊ ሆነስ ግን፥ድሉ እንዴትም ተገኘ እንዴት-የጥንካሬ ዉጤት እንጂ የአጋጣሚ ግኝት አይደለም።
«አራቱ ቡድናት ለግማሽ ፍፃሜ መድረሳቸዉ አጋጣሚ አይደለም»የጀርመን ብሔራዊ ቡድን እና የባየሩ ተጫዋች ቶማስ ሙለርም የራሱ ክለብም ሆነ የዶርት ሙንዶችን ድል የጥረታችን ዉጤት፥ የገባነዉ ቃል ገቢራዊነት እማኝ ይለዋል።
«ለግማሽ ፍፃሜ በማለፋችን ደስተኞች ነን።አሁን የምንጫወተዉ ለጀርመን ብሔራዊ ቡድን ሳይሆን ለባየር ሙዉኒክ ቢሆንም ያገኘነዉ ዉጤት የጀርመን እግር ኳስን ለማሳደግ ባለፉት ዓመታት በገባነዉ ቃል መሠረት የተገኘ ነዉ።»
የሙለር ቡድን ትናንት ሁለት ለዜሮ የቀጣዉ የኢጣሊያዉ ጁቬንትስ ቱሪን በተለይ በመጀሪያዉ አጋማሽ ጥሩ ተጫዎቶ ነበር።ዴሎ ስፖርቶ የተሰኘዉ የኢጣሊያ ጋዜጣ ዛሬ እንደዘገበዉ ግን «ከአዉሮጳ ደረጃ ለመድረስ ብዙ ይቀረዋል።»
የደረጃዉ መለኪያ፥አሁን አራቱ ክሎቦች ናቸዉ። ካራቱ-ሐይለኞች፥የሐይለኞች ሐይለኛ የሚሆነዉ ማን ነዉ? ነዉ-የከእንግዲሁ ጥያቄ።የባየር አሰልጣኝ ዩፕ ሔይንከስ «ያሻዉ አይጣ» አይነት ይላሉ።«ጥሩ እንጫወታለን፥ የተዋጣለት እግር ኳስ።ከማን ጋር እንደምንገጥም ግን ወደፊት እናያለን።በአየነ ቁራኛ የምንጠብቀዉ፥ ሪል ማድሪድን ይሁን ባርሴሎናን ወይም ዶርትሙንድን አናዉቅም።»
ከአራቱ ቡድናት ማን ከማን ጋር እንደሚጋጠም ነገ ንዮን-ሲዊዘርላንድ በሚወጣዉ ዕጣ ይበየናል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ