1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን ኤኮኖሚ፧ በጠበብት ሲገመገም፧

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 9 1997

በየወቅቱ የጀርመንን የኤኮኖሚ ይዞታ የሚገመግሙ ፮ ተቋማት፧ ዛሬ በርሊን ላይ የጥናታቸውን ውጤት ሲያቀርቡ እንዳሉት፧ የአገሪቱ ኤኮኖሚ ባሁኑ መጸው እንደተጠበቀው ሳይሆን ቀርቶ በአስተማማኝ ሁኔታ የሚያንሠራራበት ምልክት አልታየም። ባለፉት ፫ ዓመታት መንቀሳቀስ ተስኖት የቆየው፧ የጀርመን ኤኮኖሚ፧ ባለንበት፧ 2004 ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት በ 1.8 ከመቶ ሲሆን ያደገው፧ በመጪው 2005 ዓ ም፧ የበርሊን የኤኮኖሚ ምርምር ነክ ተቋም እንደሚገምተው ወደ 2 ከመቶ ከፍ ማለቱ አ

https://p.dw.com/p/E0fH
ምስል dpa

ይቀርም።

አብዛኞቹ የኤኮኖሚ ምርምር ነክ ተቋማት፧ የሆነው ሆኖ ከ 1.5 ከመቶ የላቀ ዕድገት ሊመዘገብ እንደማይችል ከመተንበያቸውም በተደቀነው የነዳጅ ዘይት ዋጋ መናር ሳቢያ፧ የሚተበቀው የኤኮኖሚ እመርታ እውን የመሆኑ ዕድል፧
እንደሚያጠራጥር ሳይተቁሙ አላለፉም። የዶቸ ቨለ ራዲዮ ባልደረባ Karl Zawadzky እንዳለው በሀገር ውስጥ ያለው የኤኮኖሚ እንቅሥቃሴ የሚጠበቀውን ያህል አይደለም። የጀርመን ኤኮኖሚ የተደላደለው ባለው ወደውጭ በሚላከው የኢንዱስትሪ ምርት-ነክ አመርቂ ገበያ ነው። በመገባደድ ላይ ባለው 2004 ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት፧ ጀርመን ለውጭ ገበያ ያቀረበችው ምርቷ፧ ፲ ከመቶ ያህል ከፍ ብሏል። ላቅ ያለ ምርት ለውጭ ገበያ በማቅረብ፧ ጀርመን ወደር ያልተገኘላት ሀገር ናት። ከዓለም ህዝብ አንድ ከመቶ ያህል የሚሆነውን ያካተተች ሀገር በዓለም ዙሪያ ፲ ከመቶውን የውጭ ገበያ መቆጣጠሯ፧ የኤኮኖሚዋን ጥንካሬ፧ በዓለም አቀፍ ደረጃም ያላትን ብርቱ የመወዳደር ችሎታ ነው የሚያስመሠክረው።
በኦፐል የተሽከርካሪዎች ፋብሪካና በካርሽታት የሸቀጣ-ሸቀጥ መድብሮች የደረሰው ውዝግብ የአገሪቱን መሠረታዊ ኤኮኖሚ የሚጎንጥ አይደለም። የጀርመን ዐቢይ ችግር የሥራ አጥ ዜጎቿ ብዛት ነው። ከ ፬ ሚልዮን በላይ ነው! ፌደራሉ መንግሥት፧ ሰፊ ጥረት በማድረግ የሥራ አጦችን ክፍያ፧ የማኅበራዊ ኑሮን ድጎማ፧ በተሃድሶ ለውጥ ለማሻሻል፧ እርምጃ ወስዷል። ለረጅም ጊዜ ሥራ አጥተው የቆዩ ወደ ሥራ መሥክ የሚሠማሩበትን እርምጃ በሰፊው በመደገፍ፧ በራሳቸው ጥረት፧ ሥራ የሚያንቀሳቅሱትንም በማበረታት፧ ሥራ አጦችም፧ ኩባንያዎችም የሚጠቀሙበት ሁኔታ መኖሩ፧ ታውቋል።
ጀርመን፧ ተጨማሪ የሥራ መስኮች ከማስገኘቷ በፊት፧ ከ ፪ ከመቶ በላይ የኤኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገብ ይኖርበታል። በሌሎች አገሮች፧ የቀጣሪና-ተቀጣሪ ግንኙነት የሠራተኛም መብት የተመጠነ ሲሆን፧ ዝቅተኛ የኤኮኖሚ ዕድገት እያሳዩም ቢሆን ተጨማሪ የሥራ መስኮችን ክፍት ያደርጋሉ። በታኅሳስ ወር ማለቂያ ገደማ ተግባራዊ የሚሆነው የተሃድሶ ለውጥ እርምጃ የሥራ አጦችን ቁጥር ለመቀነስ፧ በእርግጥ ተፈላጊ ነው። ይህ ችግር መፍትኄ ካልተገኘለት ግን፧ ጀርመን አውሮፓ ውስጥ በኤኮኖሚ እንቅሥቃሴ ረገድ ዳካሪ አገር ሆና እንዳትቀር ያሠጋታል። እርግጥ ነው የዚህ ተቃራኒ የሚጠበቅ ነው ሲሆን፧ ጀርመን ለራሷ ጥቅምም ስለሚበጃት፧ የአውሮፓ ኤኮኖሚ ዕድገት አንቀሳቃሽ ሞተር መሆን ይኖርበታል። የሠራተኞች የሥራ ጊዜ የሚጨምርበት ሁኔታ ከተፈጠረ፧ ኤኮኖሚው በትንሹም ቢሆን ማደጉ አይቀሬ ነው።
የኤኮኖሚ ገምጋሚዎቹ ተቋማት እንደሚሉት፧ ለውጭ ገበያ የሚቀርበው ምርትና የአገር ውስጥ ፍጆታ ከቀነሰ፧ ሥራ ላይ የሚውለው ንዋይ፧ መጨመሩ የማይቀር ነው። ኩባንያዎች ባለፉት ዓመታት ያጋጠመውን ውዝግብ ተገንዝበው፧ ኢንዱስትሪውን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግና የማምረት አቅሙንም ለማጠናከር መጣራቸው አልቀረም። ይህም፧ በመጠኑም ቢሆን፧ ለአጠቃላዩ የኤኮኖሚ መደላደል በጅቷል። ሂደቱ አዎንታዊ ነው። አሁን የሚቀረው፧ በአገር ውስጥ የፍጆታ መጠን የሚሻሻልበትና የሚጨምርበት ሁኔታ ነው። ይህም ሲሆን፧ የኤኮኖሚው እንቅሥቃሴ እየፈጠነ መፈርጠሙ ውሎ አድሮ፧ የሚታይ ይሆናል።