የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ከጠ/ሚ ዐቢይ ጋር ስኬታማ ዉይይት አካሄዱ
ማክሰኞ፣ ጥር 21 2011ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ከጀርመኑ ፕሬዚዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ጋር ዉይይት አካሄዱ። ሁለቱ መሪዎች በዉይይታቸዉ ሃገራቱ በኤኮነሚ ጉዳይ ላይ የሚኖራቸዉ ሚና ላይ ተወያይተዋል። የጀርመን ፌደራል ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር፤ ለአፍሪቃ እግዳ አይደሉም። ኢትዮጵያንም ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር በነበሩበት ዘመን በ2014 እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ጎብኝተዋታል።ያዉቋታል።ኢትዮጵያ ዉስጥ የተደረገዉን ለዉጥም በቅርብ ይከታተላሉ።ለዉጡ እና እርምጃዉን «ከኢትዮጵያ ድንበር አልፎ የሚያንፀባርቅ፣ ለአፍሪቃ አብዮታዊ ዉሳኔ።» ይሉታል። ለዉጡ ፈተና እንዳለዉም አላጡም።«የዋሕ አይደለንም» ሲሉ ወደ ኢትዮጵያ ከማቅናታቸዉ በፊት ለ«DW» ጋዜጠኞች በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናግረዉ ነበር። በመቀጠል ሽታይን ማየር አፍሪቃን ሲጎበኙ ያሁኑ ሶስተኛዎ ነዉ። ከዚሕ ቀደም ጋና፣ ጋምቢያ፣ ደቡብ አፍሪቃ እና ቦትስዋና ነበሩ። እንደ ጋምቢያ ሁሉ ኢትዮጵያ ዉስጥ አስገራሚ ዴሞክራሲያዊ ለዉጥ ተደርጓል። ኢትዮጵያን እንዴት ነዉ የሚገመግሙት? ተብለዉ ለተጠየቁት
ፕሬዝደንቱ ሲመልሱ የተለየ ነዉ። ምክንያቱም ኢትዮጵያን ስጎበኝ የመጀመሪያዬ አይደለም። ሐገሪቱን በተወሰነ ደረጃ አዉቃታለሁ። እርግጥ ነዉ ያየኋት በሌላ ጊዜና ፖለቲካዊ ሁኔታ ዉስጥ እያለች ነበር። ባለፉት ጥቂት ዓመታት ዉስጥ ኢትዮጵያዉያን በአዲሶቹ መሪዎች አማካይነት ወደ አዲስ ሥርዓት በሚያሸጋግር አስደናቂ ለዉጥ እና ተሐድሶ ላይ ናቸዉ። ፕሬዝደንት ሳሕለ ወርቅ ዘዉዴና ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ ሐገሪቱን እንድጎበኝ ሲጠይቁኝ ግብዣዉን ሳላመነታ የተቀበልኩትም ለዚሕ ነዉ።ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚደረገዉን የለዉጥ ሒደት ከሩቅ ሆኖ ክብር መስጠት ብቻ ሳይሆን፣ እኛ አዉሮጳዊያንና ጀርመናዊያን፣ እዚያዉ ስፍራዉ ተገኝተን የዴሞክራሲያዊውን የለዉጥ ጉዞ ማበረታት ይገባናል ብዬ አምናለሁ። ለዚሕም ነዉ ኢትዮጵያን የምጎበኝበት ትክክለኛዉ ጊዜ አሁን ነዉ የምለዉ።» ብለዉ ነበር። ቀደም ሲል ከኢትዮጵያዋ ፕሬዚዳንት ሳህለ ውርቅ ዘውዴ ጋር የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ቫልተር ሽታይንማየር ይዘዋቸዉ ከሄዱት ባለወረቶችና ከኢትዮጵያ የንግድ ማህበረሰብ አባላት ጋው ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።
አዜብ ታደሰ