የዶይቼ ቬለ ልዩ ዘገባ፤ አፍሪቃ ስለምን ትራባለች?
ሰኞ፣ ጥቅምት 6 2010ምን እንደተፈጸመ ዘግይታችሁ ከምትረዱባቸው ቅጽበቶች አንዱ ነው። የሕክምና ዶክተር እና ነርስ አንድ ልጅ መልሶ ነፍስ እንዲዘራ ይጥራሉ። ከአልጋዋ ላይ የተቀመጠችው እናት ምንም አይነት እንቅስቃሴ አታደርግም። ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ይደረግ የነበረው ጥረት እንዲቆም ዶክተሩ ትዕዛዝ አስተላለፉ። በክፍሉ ውስጥ የጸጥታ ስቅስቅታ ይደመጥ ጀመር። ከዚያ ለቅሶ ተከተለ። ሕፃኑ የተኛበት አልጋ በመጋረጃ ተሸፈነ። ከዚያ በኋላ ምን እንደተከተለ ያየንው ነገር የለም።
ይኸ በሰሜናዊ ኬንያ የታዘብንው ክስተት በረሐብ በተመቱ የአፍሪቃ አገሮች ባደረግንው የጥናት ጉዞ እጅጉን አስቸጋሪው ስሜታዊ ወቅት ነበር። የረሐብ ሥጋት ያንዣበበባቸው 26 ሚሊዮን ሰዎች ዝም ብሎ ቁጥር ብቻ አለመሆናቸውን ግልጥ አድርጎ የሚያሳይ ለብዙዎቹ ሰዎችም ረሐብ ከሥጋት በላይ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነበር። ትንሿ ልጅ በኬንያ ሆስፒታል የሞተችው ታክሞ በማይድን በሽታ አልነበረም። ሕጻኗ የሞተችው ለረጅም ጊዜ ምግብ ባለመቅመሷ ነበር።
ረሐብ አርዕስተ-ዜና አይሆንም
የዶይቼ ቬለ ዘጋቢዎች የረሐብ ቀውስን ለመፈተሽ በርካታ የአፍሪቃ አገሮችን አቆራርጠዋል። የልማት ረጂዎችን፤ ባለሙያዎችን ከሁሉም በላይ የጉዳቱን ምክንያቶች መርምሮ ለማግኘት በረሐብ የተጠቁ ሰዎችን አነጋግረዋል።
ከጥቂት ጊዚያት በፊት የእርዳት ድርጅቶች በአፍሪቃ ስላለው ረሐብ ማስጠንቀቂያ መስጠታቸው በጉዳዩ ላይ የሚያተኩሩትን የዶይቼ ቬለ ተከታታይ ዘገባዎች ወቅታዊ ያደርጋቸዋል። የእርዳታ ድርጅቶቹ ተስፋፊ ድርቅ በአፍሪቃ እና በየመን ካለፉት አስር አመታት እጅግ የከፋ የረሐብ መቅሰፍት ሊያስከትል እንደሚችል አስጠንቅቀው ነበር። ወዲያውኑ ግን ነባራዊው ሁኔታ ያን ያክል መሻሻል ባያሳይም የተተነበየው ቀውስ ርዕሰ-ዜና መሆኑ ቀረ። ቀውሱ በከፋባቸው ደቡብ ሱዳን እና እና ሶማሊያ 14 ሚሊዮን ሰዎች ዛሬም ድረስ የምግብ እርዳታ ጥገኛ ናቸው።
ሰዎች እንደ ዋንኛ ምክንያት
እነዚህን አስደናቂ ሁኔታዎች የፈጠረው ምንድነው? ለዚህ ጥያቄ ዘገባው የማያሻማ ምላሽ አለው። ሰዎች ሳይሆኑ ተፈጥሮ ነው። ዓለም አቀፍ የከባቢ አየር ለውጥ፣ መጠነ ሰፊ የደን ጭፍጨፋ እና ወደ አንድ ጎን ያዘነበለ የምርት ሒደት በጠባብ የእርሻ መሬት ለተወሰኑት የአፍሪቃ ገበሬዎች ሕይወትን ፈታኝ አድርጎባቸዋል። ነገር ግን ፖለቲካዊ ግጭቶች የባሰ ዳፋ አላቸው። በረሐብ አብዝተው የተመቱት እንደ ናይጄሪያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ሶማሊያን የመሳሰሉ አገሮች በርስ በርስ ጦርነት ተዘፍቀዋል፣አሊያም ከሽብርተኞች ጋር ውጊያ ላይ ናቸው። በእነዚህ አገራት መንግሥታቱ የጤና አገልግሎት፣ ትምህርት፣ ወይም የተረጋገጠ ጸጥታ የመሳሰሉ መሰረታዊ ግልጋሎቶችን ማቅረብ ተስኗቸዋል። በዚህ ፈንታ ላቅ ያለ ሐብት ባላቸው አገራት ጥቂት ልሒቃን የግል ኪሳቸውን በመሙላት ተጠምደዋል።
ጥንቃቄ ያልራቀው ተስፈኝነት
ቢሆንም የዶይቼ ቬለ ዘጋቢዎች ተስፋን የሰነቁ ታሪኮችን ይዘው ተመልሰዋል። ለምሳሌ ያክል ለ20 አመታት ከዘለቀ የርስ በርስ ጦርነት በኋላ ሶማሊያ በጎርጎሮሳዊው 2017 ዓ.ም. መጀመሪያ አዲስ መንግሥት አግኝታለች። ይኸ በርካታ ታዛቢዎችን ባለተስፋ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። በሁሉም ቦታ የዶይቼ ቬለ ዘጋቢዎች ልዩ በሆኑ አጋጣሚዎች ከግል አቅማቸው ባሻገር መመልከት የቻሉ፤ተስፋም ያልቆረጡ ሰዎች አግኝተዋል። ምክንያቱም ሰዎች የረሐብ መነሾ ምክንያት ብቻ ሳይሆኑ መፍትሔ ጭምር ናቸው። ከጥቅምት 6 ቀን 2010 ጀምሮ ዶይቼ ቬለ በረሐብ ላይ የሰራቸውን ተከታታይ ልዩ ዘገባዎች በየቀኑ በራዲዮ፤ በቴሌቭዥን እና በድረ-ገፅ www.dw.com መከታተል ትችላላችሁ።