የዶቼቬለ አካዳሚ በኢትዮጵያ ለጋዜጠኞች የሰጠው ሥልጠና
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 8 2007ማስታወቂያ
የዶቼቬለ የጋዜጠኞች ማሠልጠኛ ተቋም( ዶቼቬለ አካዳሚ )አዲስ አበባ ውስጥ ካለፈው ሰኞ አንስቶ ለጋዜጠኞች ሥልጠና እየሰጠ ነው ። በምርጫ አዘጋገብ ላይ ባተኮረው በዚሁ ዐውደ ጥናት ላይ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች የመጡ የመንግሥትና የግል መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞች ተካፍለዋል ። ዶቼቬለ አካዳሚ የኢትዮጵያ ፕሬስ ክለብ ከተባለው የጋዜጠኞች መድረክ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ይኽው ዐውደ ጥናት እስከ ነገ ይቀጥላል ። በዐውደ ጥናቱ ላይ በአሰልጣኝነት የተካፈሉት በምሥራቅና ምዕራብ አፍሪቃ እንዲሁም በሌሎችም የዓለም ክፍሎች የካበተ የማስተማር ልምድ ያላቸው የአካዳሚው ባልደረባ ጀርመናውያን ጋዜጠኞች ናቸው ። ዘንድሮ 50 ዓመት የደፈነው ዶቼቬለ አካዳሚ በኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት ለጋዜጠኞ ሥልጠና ሲሰጥ ነበር ። የአሁኑ ሥልጠና ግን ከጎርጎሮሳዊው 2007 ዓም ወዲህ አካዳሚው በኢትዮጵያ ያካሄደው የመጀመሪያው ሥልጠና መሆኑ ነው ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ
አርያም ተክሌ