የድምፃዊ ሐጫሉ ሁንዴሳ ቀብር በአምቦ ይፈጸማል ተባለ
ማክሰኞ፣ ሰኔ 23 2012ማስታወቂያ
የድምፃዊ ሐጫሉ ሁንዴሳ አስከሬን አምቦ ደረሰ። የድምፃዊው አስከሬን በአዲስ አበባ እንዲቆይ ግፊት ቢደረግም ወደ ትውልድ ከተማው አምቦ መጓዙን ዶይቼ ቬለ አረጋግጧል። ከጳውሎስ ሆስፒታል ወጥቶ ወደ አምቦ በመጓዝ ላይ የነበረው አስከሬን በቡራዩ ከተማ አስተዳደር ኬላ የተባለ ቦታ በወጣቶች ተቃውሞ እንዲዘገይ ተደርጓል። ወጣቶች የቀብር ሥነ ሥርዓቱ በአዲስ አበባ መካሔድ አለበት የሚል አቋም እንደነበራቸው የዶይቼ ቬለ ዘጋቢ አረጋግጧል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ ከአርቲስቱ ቤተሰቦች ጋር ጥብቅ ውይይት ተደርጎ ከስምምነት በመደረሱ ቀብሩ በትውልድ ቀዬው አምቦ እንዲከናወን መወሰኑን ተናግረዋል።አቶ ሽመልስ እንዳሉት አባገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና የክልሉ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የተካተቱበት የቀብር አስፈፃሚ ኮሚቴ ተዋቅሯል። በኦሮሚያ ክልል ለአምስት ቀናት ሰንደቅ አላማ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ውሳኔ ተላልፏል። ድምፃዊ ሐጫሉ ሁንዴሳ የጀግና አሸኛኘት እንደሚደረግለት የክልሉ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።
ስዩም ኃይሉ
አዜብ ታደሰ
እሸቴ በቀለ