የደረቅ ደን ሃብት በኢትዮጵያ
ማክሰኞ፣ መጋቢት 20 2008ሆኖም ለጣዉላ ምርት ሲባል የሚቆረጠዉ እና ለማገዶ እንጨትነት የሚዉለዉ በመበርከቱ ስብጥርና አይነቴዉን እያመናመነ ለአደጋ እያጋለጠዉ እንደሆነ ነዉ የሚገለጸዉ። ቆላማዉ አካባቢ በበረሃነቱና እና በሙቀቱ ኃያልነት እንጂ በዉስጡ ይህን ያህል የተፈጥሮ ሃብት ማከማቸቱ ላይታወቅለት ይችላል።
ምንም እንኳን አብዛኛዉ የደን ሃብት የቆላዉ ደረቅ ደን ነዉ ቢባልም በእርሻ መስፋፋትና ሰፈራ ምክንያት ለአደጋ መጋለጡንም ባለሙያዉ አመልክቷል። ከቅርብ አስርት ዓመታት ወዲህ የደን ምርምርና ጥናቱ የቆላ ደረቅ ደኖች ላይ ማተኮር ሲጀርም የሚሰጡት የኤኮኖሚም ሆነ የአካባቢ ጥበቃ ጥቅም ትኩረት እንዳገኘም ተጠቅሷል። የቆላ አካባቢ ደኖች ለአርብቶ አደር እና ለአርብቶ አደር አርሶ አደሩ ማኅበረሰብ የሚኖራቸዉን ማኅበራዊና ኤኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ለማሳደግ የደረቅ ደን አስተዳደር ላይ ለዶክትሬት ዲግሪዉን እዚህ ጀርመን ድሬዝደን ቴክኒዎሎጂ ዩኒቨርሲቲ፤ በአካባቢ ተፈጥሮ ሳይንስ ፋኩሊቲ ለአራት ዓመታት ጥናት ያካሄደዉ ዶክተር አደፍርስ ወርቁ ስለኢትዮጵያ ደን ሲነገር ትልቁ ደን ያለዉ ቆላማዉ አካባቢ እንደሆነ ያስረዳል።
የቆላ አካባቢ ደረቅ ደን ለማኅበረሰቡም ሆነ ለአካባቢ ተፈጥሮ የሚያደርገዉ አስዋጽኦ በዚህ ብቻ አይገደብም። እንደተመራማሪዉ ጥቅማቸዉ ዘርፈ ብዙ ነዉ፤ በዚያም ላይ ተገቢዉን አሰራር በማሻሻል ደግሞ የበለጠም መጠቀም ይቻላል።
የቆላ ደረቅ ደኖች ለኤኮኖሚም ሆነ ለአካባቢ ተፈጥሮ ጥበቃ ያላቸዉን ከፍተኛ ጠቀሜታ የሚያመላክቱ ጥናቶች በተለያዩ ጊዜያት ቀርበዋልል። እነዚህን ደረቅ ደኖች እየተንከባከቡ ከእንስሳት እርባታዉ ጋር በማቀናጀት የተሻለ ጥቅም ማግኘት የሚያስችል ተስፋ ቢኖርም ብዙ መሠራት ያስፈልጋል።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ