የዘንድሮው የአውሮፓ ሃገራት የሙዚቃ ውድድር
ሐሙስ፣ ግንቦት 27 2007ከጎርጎረሳዉያኑ 1956 ጀምራ ይህን የሙዚቃ ዉድድር ተካፋይ የሆነችዉ ጀርመን በበኩልዋ በዘንድሮዉ ዉድድር ዉራ መዉጣትዋ ይህን የሙዚቃ ዉድድር መድረክ በሚከታተሉ ጀርመናዉያን የሙዚቃ አፍቃሪዎች ዘንድ ከፍተኛ የሃዘን ድባብን ነበር የፈጠረዉ፤ በበዕለቱ ዝግጅታችን ዘንድሮ ስለተካሄደዉና በዓለማችን ግዙፍ እንደሆነ ስለሚነገርለት Eurovision Song contest «ይሮ ቪዥን ሶንግ ኮንቴስት» ስለተሰኘዉ የሙዚቃ ዉድድር መድረክ ቅንብር ይዘናል መልካም ቆይታ።
ዘንድሮ ለስድሳኛ ጊዜ የተካሄደዉ ግዙፉ የአዉሮጳ ሃገራት የሙዚቃ ዉድድር Eurovision Song contest አሸናፊ ስዊድናዊ ሙዚቀኛ በእንጊሊዘኛ ቋንቋ ያቀነቀነዉ ሙዚቃዉ «ሄሮ ይሰኛል ። «ዘንድሮ ኦስትርያ መዲና ቬና ላይ በተካሄደዉ ዉድድር ላይ ከሃያ ሰባት የተለያዩ የዓለም ሃገራት የተዉጣጡ ከያኒዎች ለጆሮ የሚጥም ሙዚቃን ለዉድድር ይዘዉ ቢቀርቡም የሃያ ዘጠኝ ዓመቱን ስዊድናዊ የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ Måns Zelmerlöw «ሂሮ» ከተሰኘዉ ሙዚቃ ሊበልጡት አልቻሉም፤ በሙዚቃዉ ጣጥሎአቸዉ አልፎአል» ሲሉ የተለያዩ የብዙሃን መገናኛዎች በማወደስ ዘግበዉለታል።
Eurovision Song contest የተሰኘዉ የሙዚቃ ዉድድር አዉሮጳዉያን እርስ በርስ ጦርነትን አቁመዉ ለጋራ መተሳሰር እና መግባባትና በመደጋገፍ የጀመሩት ያጋራ መድረክ ሲሆን ሁለተኛ ዓለም ጦርነት በተጠናቀቀ በአስራ ሁለተኛ ዓመቱ እንደ አዉሮጳዉያን አቆጣጠር 1956 ዓ,ም የአዉሮጳ የራድዮ ስርጭት ማኅበር ለመጀመርያ ግዜ ያቋቋመዉ የሙዚቃ ዉድድር እንደሆነም ጽሁፎች ይጠቁማሉ። ነገሩ አዉሮጳዉያን ተሰኘ እንጂ የራድዮ ማህበር አባል ሃገራት ሁሉ የሚሳተፉበት ሲሆን የማህበሩ አባላት እስራኤልን የእስያ አገራትን እንዲሁም የሰሜን አፍሪቃ ሃገራትንም ሁሉ ያጠቃልላል። እንደዉም ዘንድሮ ከአዉሮጳ እርቃ የምትገኘዉ አዉስትራልያም ለመጀመርያ ጊዜ ይህን ዉድድር ተካፍላለች።
ኦስትርያ ዘንድሮ ይህን ግዙፍ የሙዚቃ ዉድድር ለማዘጋጀት የበቃችዉ በአለፈዉ ዓመት ዴንማርክ መዲና ኮፐን ሃገን ላይ የተካሄደዉን 59 ኛ የአዉሮጳ የሙዚቃ ዉድድር «ኮንቺታ ቮርስት» በተሰኘዉ ሪዛም ጨጉረ ዘላጋ ቀሚስ አጥላቂ ከያኒ አሸናፊነትን በማግኘቱ መሆኑ ይታወቃል። እዚህ አዉሮጳ እንደዉም በወንድ ሳይሆን የሚጠሩት ተባታይ አድርገዉ ነዉ የሚያዩዋት። ወደ ጀመርነዉ ርዕስ ስንመለስ ታድያ ኦስትርያ አገርዋ ላይ ይህን የዓለም ግዙፍ የሙዚቃ ዉድድር ስታዘጋጅ ከጎርጎረሳዉያኑ 1967 ዓ,ም በኋላ ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ አዘጋጅ መሆኗ ነዉ።
ዘንድሮ በተዘጋጀዉ በስድሳኛዉ የዓለም ግዙፍ የሚዚቃ ዉድድር ላይ ሁለተኝነትን ያገኘችዉ የሩስያዋ ሙዚቀኛ ፖሊና ጋጋሪና "A Million Voices" ሚሊዮን ድምፆች የተሰኘዉን ሙዚቃዋን ይዛ በመቅረብ ነዉ።
የዛሬ ሁለት ሳምንት ግድም ኦስትርያ ላይ በተካሄደዉ ስድሳኛ የአዉሮጳ ሃገራት የሙዚቃ ዉድድር ላይ «ግራንዴ አሞሪ » በተሰኘ ሙዚቃቸዉ ሶስተኝነት ያገኙት ከኢጣልያ የመጡት ሙዚቀኞች ነበሩ። እስከ አስረኛ ደረጃን ከያዙት ሃገራት መካከል የሌትላንድና የቤልጄየም ሙዚቀኞች በመድረክ ይዘዉ በቀረቡት ሙዚቃ በዓለም የሙዚቃ አፍቃሪዎች ዘንድ እዉቅናን እንዳገኙ ተመልክቶአል።
አርሜንያ በዘንድሮዉ ዉድድር ባቀረበችዉ ሙዚቃ አስራ ስድስተኛ ደረጃን የያዘች ሲሆን በመድረኩ ከቀረቡት ስድስት ሙዚቀኞች መካከል ትዉልደ አርሜንያዊዉ ኢትዮጵያዊ ቫሄ ቴልቢያን ይገኝበታል ።
ቫሄ ዉድድሩን አጠናቆ ወደ መኖርያ ሃገሩ ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሰ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዞአል። ኢትዮጵያዊዉ ቫሄ የዉድድር መድረኩ ድባብ በቃላት ሊገለፅ የማይችል እጅግ እፁብ ድንቅ የነበር መሆኑን አጫዉቶናል።
እስከ ዛሪ በዚህ ዉድድር ከአፍሪቃ ሞሮኮ እንደ ጎርጎረሳዉያን አቆጣጠር 1980 ዓ.ም ላይ ተሳታፊ ነበረች። የአዉሮጳዉ የራድዩ ስርጭት ማኅበር አባል ሆነዉ በዚህ የሙዚቃ ዉድድር እስከ ዛሬ ያልተሳተፉ ሃገራት አልጀርያ፤ ቱኒዚያ፤ ሊቢያ፤ ግብጽ ዮርዳኖስና ሊባኖን ይገኙበታል። የአዉሮጳ የራድዩ ስርጭት ማህበር አባላት ወደ ሰባ አምስት ሃገራት ግድም ሲሆኑ ሃምሳ ስድስቱ አዉሮጳ ዉስጥ የሚገኙ ቀሪዎቹ ደግሞ ሰሜን አፍሪቃና እስያ የሚገኙ ሃገሮች መሆናቸዉን ጽሑፎች ይጠቁማሉ። ዘንድሮዉ ይህን ዉድድር ለመጀመርያ ጊዜ ተሳትፊ ሆና አምስተኛ ደረጃን ያገኘችዉ አዉስትራልያ በዉድድሩ እንደምትሳተፍ ቀደም ብሎ ማኅበሩ ይፋ አድርጎ ነበር።
ጀርመን እና ኦስትርያ ዘንድሮ በተካሄደዉ ስድሳኛ የአዉሮጳ ሃገራት የሙዚቃ ዉድድር እድል አልቀናቸዉም። ሁለቱም ሃገራት ምንም ነጥብን አላገኙም ከዉድድሩ የወጡት በዜሮ መሆኑን ተከትሎ በብዙኃን መገናኛ ርዕሱ ደምቆ ነዉ የሰነበተዉ። ጥንት በጀመረዉ በዚህ የሙዚቃ ዉድድር ጀርመን በዜሮ ስትወጣ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑም ተመልክቶአል። ዘንድሮ እንዲሁም ጥንት በጎርጎረሳዉያኑ 1964 እና 1965 ዓ,ም። «ብላክ ስሞክ» የተሰኘዉን ሙዚቃዋን ይዛ ጀርመንን ወክላ የቀረበችዉ ወጣትዋ ጀርመናዊት ሙዚቃኛ አነ ሶፊ፤ ምንም እንኳ በዚህ መድረክ ምንም ነጥብን ባታመጣም በሙዚቃ ሥራዋ እንደምትቀጥል ተናግራለች።
በዚህ የዉድድር መድረክ አሸናፊዎች ወደ 80 ሽህ ይሮ እንደሚያገኙ ተመልክቶአል። በሌላ በኩል አሸናፊዎች በተለያዩ የአዉሮጳ አገራት ስራዎቻቸዉን በማስተዋወቅና የራድዮ ቃለ መጠይቅ በማድረግ እንዲሁም ራስን በማስተዋወቅ የሙዚቃ ስራቸዉን በመሸጥ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያገኙበት መድረክን እንደሚያገኙም ይታወቃል።
እጎአ 1956 አ.ም ለመጀመርያ ግዜ በስዊዘርላንድ ሉጋኖ ዉስጥ የተካሄደዉ ይህ የአዉሮጳ የሙዚቃ ዉድድር መድረክ በዓለም ዙርያ ተወዳጅ የሆኑ ሙዚቀኞችን አፍርቶአል። ለምሳሌ በዓለም ታዋቂዋ የፖፕ የሙዚቃ ተጫዋች ሴሊን ዲዮን የአዉሮጳዉ የሙዚቃ የዉድድር መድረክ ለ 33ኛ ግዜ በዘረጋዉ የዉድድር መድረክ ላይ ተሳትፋ ባቀረበችዉ የፈረንሳይኛ ሙዚቃ በዓለም የሙዚቃ መድረክ እዉቅናን አግኝታ ኮከብ ሙዚቀኛ ለመሆን መብቃትዋ ይታወቃል።
ABBA በመባል የታወቀው የስዊድን የፖፕ ሙዚቃ ባንድ አባላትም፤ እ ጎ አ በ1974 ዓ.ም፤ waterloo የተሰኘዉን ሙዚቃ አቅርበዉ በማሸነፍ ተደናቂነትን አግኝተዋል።
40 ሃገራት ለዉድድር ቀርበዉ በማጣርያ ሃያ ሰባት ሃገራት ለአሸናፊነት ስለተወዳደሩበት ስለ 60 ኛዉ የአዉሮጳ ሃገራት የሙዚቃ ዉድድር «ይሮ ቪዥን ሶንግ ኮንቴስት» ያጠናቀርነዉ መሰናዶ እስከዚሁ ነበር። አድማጮች መልካም ምሽት እያልኩ በሚቀጥለዉ ሳምንት በሌላ ርዕስ እስክንገኛኝ ልሰናበት አዜብ ታደሰ ነኝ ጤና ይስጥልኝ።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ